ኮርፖሬሽኑ ለአቅመ ደካሞች ማዕድ አጋራ

አዲስ አበባ፣ መስከረም 1 ቀን 2019 ዓ.ም (ኢግሥኮ)፦ የኢትዮጵያ የግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን የ2019 ዘመን መለወጫን ምክንያት በማድረግ በኮልፌ ቀራንዮ ክፍለ ከተማ ወረዳ 1 በሚገኘው የተስፋ ብርሃን ምገባ ማዕከል ለአቅመ ደካሞች ማዕድ አጋራ።
መስከረም 1 ቀን በተካሄደው የማዕድ ማጋራት መርሐ ግብር ላይ የተገኙት የኮርፖሬሽኑ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ወ/ሮ የሺእመቤት ነጋሽ፣ ተቋሙ የግብርና ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ከሚያደርገው ዘርፈ ብዙ ጥረት ጎን ለጎን ለማኅበራዊ ኃላፊነት ሥራዎች ትኩረት ሰጥቶ እየሠራ እንደሚገኝ ገልጸዋል።
ከዚህ አኳያ ኮርፖሬሽኑ ለሀገር ውለታ የዋሉ አረጋውያንን፣ አቅመ ደካሞችን፣ አካል ጉዳተኞችን፣ ሴቶችንና ሕፃናትን እንዲሁም አስታዋሽ የሌላቸውን ዜጎች ለመደገፍ፣ ከጎናቸው ለመቆምና በዓሉን በደስታ እንዲያሳልፉ ለማድረግ ማዕድ ማጋራቱን አስታውቀዋል።
በዕለቱ በተዘጋጀው መርሐ ግብር ላይ የኮርፖሬሽኑ የበላይ አመራሮች፣ የኮልፌ ቀራንዮ ክፍለ ከተማ ም/ዋና ሥራ አስፈጻሚና የሥራና ክህሎት ጽ/ቤት ኃላፊ፣ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምገባ ኤጀንሲ ምክትል ዳይሬክተር እንዲሁም የክፍለ ከተማው እና የወረዳ 1 አስተዳደር አመራሮች ተገኝተዋል።
ኮርፖሬሽኑ ሰሞኑን በዋና መ/ቤት በፅዳት፣ በጉልበት ሥራና በካፍቴሪያ ለሚያገለግሉ እንዲሁም በአዳማ ቅርንጫፍ ጽ/ቤት የውጭ ምንዛሬ በሚያስገኘው የእጣንና የሙጫ ምርት ዝግጅት ላይ በቀን ሥራ ለተሰማሩ በአጠቃላይ ለ140 የቀን ሠራተኞች የአዲስ ዓመት በዓል መዋያ ማዕድ ማጋራቱ ይታወሳል።
###
ግብርናን ማዘመን ግባችን ነው!







































































