የኢትዮጵያ የግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን Ethiopian Agricultural Businesses Corporation

ኮርፖሬሽኑ ለአቅመ ደካሞች ማዕድ አጋራ

አዲስ አበባ፣ መስከረም 1 ቀን 2019 ዓ.ም (ኢግሥኮ)፦ የኢትዮጵያ የግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን የ2019 ዘመን መለወጫን ምክንያት በማድረግ በኮልፌ ቀራንዮ ክፍለ ከተማ ወረዳ 1 በሚገኘው የተስፋ ብርሃን ምገባ ማዕከል ለአቅመ ደካሞች ማዕድ አጋራ።

መስከረም 1 ቀን በተካሄደው የማዕድ ማጋራት መርሐ ግብር ላይ የተገኙት የኮርፖሬሽኑ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ወ/ሮ የሺእመቤት ነጋሽ፣ ተቋሙ የግብርና ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ከሚያደርገው ዘርፈ ብዙ ጥረት ጎን ለጎን ለማኅበራዊ ኃላፊነት ሥራዎች ትኩረት ሰጥቶ እየሠራ እንደሚገኝ ገልጸዋል።

ከዚህ አኳያ ኮርፖሬሽኑ ለሀገር ውለታ የዋሉ አረጋውያንን፣ አቅመ ደካሞችን፣ አካል ጉዳተኞችን፣ ሴቶችንና ሕፃናትን እንዲሁም አስታዋሽ የሌላቸውን ዜጎች ለመደገፍ፣ ከጎናቸው ለመቆምና በዓሉን በደስታ እንዲያሳልፉ ለማድረግ ማዕድ ማጋራቱን አስታውቀዋል።

በዕለቱ በተዘጋጀው መርሐ ግብር ላይ የኮርፖሬሽኑ የበላይ አመራሮች፣ የኮልፌ ቀራንዮ ክፍለ ከተማ ም/ዋና ሥራ አስፈጻሚና የሥራና ክህሎት ጽ/ቤት ኃላፊ፣ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምገባ ኤጀንሲ ምክትል ዳይሬክተር እንዲሁም  የክፍለ ከተማው እና የወረዳ 1 አስተዳደር አመራሮች ተገኝተዋል።

ኮርፖሬሽኑ ሰሞኑን በዋና መ/ቤት በፅዳት፣ በጉልበት ሥራና በካፍቴሪያ ለሚያገለግሉ እንዲሁም በአዳማ ቅርንጫፍ ጽ/ቤት የውጭ ምንዛሬ በሚያስገኘው የእጣንና የሙጫ ምርት ዝግጅት ላይ በቀን ሥራ ለተሰማሩ በአጠቃላይ ለ140 የቀን ሠራተኞች የአዲስ ዓመት በዓል መዋያ ማዕድ ማጋራቱ ይታወሳል።
                  ###
ግብርናን ማዘመን ግባችን ነው!

የኮርፖሬሽኑ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ለቀን ሠራተኞች ማዕድ አጋሩ

አዲስ አበባ፣ ጳጉሜን 4 ቀን 2018 ዓ.ም (ኢግሥኮ):-  የ2019 አዲስ ዓመትን እና የኅብር ቀንን ምክንያት በማድረግ የኢትዮጵያ የግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን ዋና ሥራ አስፈጻሚ ለተቋሙ የቀን ሠራተኞች ጳጉሜን 4 ቀን 2018 ዓ.ም ማዕድ አጋሩ።

ዋና ሥራ አስፈጻሚዋ ወ/ሮ የሺእመቤት ነጋሽ ከተቋሙ የበላይ አመራሮች ጋር በመሆን በኮርፖሬሽኑ ዋና መ/ቤትና በአዳማ ቅርንጫፍ ጽ/ቤት ለሚያገለግሉ 140 የቀን ሠራተኞች ማዕድ አጋርተዋል።

በዕለቱ በ805 ሺህ ብር ወጪ የተገዙ ዱቄት፣ ዘይት፣ ዶሮና እንቁላል ድጋፍ ተደርጓል።

ድጋፍ የተደረገላቸው፣ ወደ ውጭ ገበያ  የእጣንና የሙጫ ምርት ዝግጅት ላይ በቀን ሥራ ላይ የተሰማሩ 45 ሴቶች እና በዋና መ/ቤት በፅዳት፣ በጉልበት ሥራና በካፍቴሪያ የሚያገለግሉ 95 የቀን ሠራተኞች ናቸው።

በዕለቱ የተቋሙ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ወይዘሮ የሺእመቤት ነጋሽ ባስተላለፉት መልእክት፣ መርሐ ግብሩ ኮርፖሬሽኑ ከቀን ሠራተኞች ጋር ያለውን አብሮነትና አጋርነት የሚያጠናክር መሆኑን ገልጸው፣ ወደፊትም አቅም በፈቀደ መጠን  አስፈላጊው ድጋፍ እንደሚደረግላቸው አስታውቀዋል።

ድጋፍ የተደረገላቸው ሠራተኞች በበኩላቸው፣ “እንደ ሠራተኛ ተቆጥረን፣ አስታዋሽ በማግኘታችን ደስተኞች ነን።” በማለት፣ ለተደረገላቸው ድጋፍ አመስግነዋል።

በኮርፖሬሽኑ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ሀሳብ አመንጪነት በተቋሙ የተጀመረው ማዕድ ማጋራት፣ የዓለም የሴቶች ቀንን ምክንያት በማድረግ ከ600 ሺህ ብር በላይ ወጪ ለ126 የኮርፖሬሽኑ የቀን ሠራተኞች ድጋፍ መደረጉ ይታወሳል።
                 ###
ግብርናን ማዘመን ግባችን ነው!

የሩሲያ የእርሻ መሣሪያዎችን ለአርሶ አደሮች ማቅረብ በሚቻልበት ሁኔታ ላይ ውይይት ተደረገ

አዲስ አበባ፣ ነሐሴ 28 ቀን 2018 ዓ.ም (ኢግሥኮ)፦ የሩሲያ ስሪት የሆኑ የእርሻ መሣሪያዎችንና ቴክኖሎጂዎችን ለኢትዮጵያ አርሶ አደሮችና ሌሎች ተጠቃሚዎች ማቅረብ በሚቻልበት ሁኔታ ላይ ነሐሴ 28 ቀን 2018 ዓ.ም  ውይይት ተደረገ።

ውይይቱ የተደረገው በኢትዮጵያ የግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን የበላይ አመራሮችና በሩሲያ የልዑካን ቡድን መካከል ነው።

በኮርፖሬሽኑ ዋና መ/ቤት በተካሄደው በዚህ ውይይት፣ ኮርፖሬሽኑ የእርሻ መሣሪያዎችንና ቴክኖሎጂዎችን ከሩሲያ ለማስመጣት ፍላጎት እንዳለው ተገልጿል።

በዚሁ ወቅት የኮርፖሬሽኑ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ወ/ሮ የሺእመቤት ነጋሽ፣  የሜካናይዜሽን አገልግሎትን ማስፋፋትና ግብርናን ማዘመን የመንግሥት ቀዳሚ አጀንዳና ትኩረት መሆኑን አስታውቀው፣ ከዚህ የተነሳ በኢትዮጵያ ከፍተኛ የእርሻ መሣሪያዎች ፍላጎት መኖሩን አብራርተዋል።

​የሩሲያ የግብርና ማሽነሪ አምራቾች በበኩላቸው የሚያመርቷቸውን የእርሻ መሣሪያዎችና ቴክኖሎጂዎች በተመለከተ ገለጻ ያደረጉ ሲሆን፣ ኮርፖሬሽኑም የሚፈልጋቸውን የማሽነሪ አይነቶችና ፍላጎቶች ለልዑካን ቡድኑ አቅርቧል።

በቀጣይ አጋርነትን ለማጠናከር የሚያስችሉ ተጨማሪ ውይይቶችንና የመስክ ጉብኝቶችን ለማድረግ የጋራ መግባባት ላይ ተደርሷል።

ሩሲያ እና ኢትዮጵያ የረጅም ዓመታት ወዳጅነት፣ ትብብርና አጋርነት ያላቸው ሲሆን፣ የኢትዮጵያ የግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን የአፈር ማዳበሪያ ከሚያስመጣባቸው ሀገራት አንዷ ሩሲያ ናት።
                ###
ግብርናን ማዘመን ግባችን ነው!

የሠራተኞች ዓመታዊ በዓል ተከበረ

አዲስ አበባ፣ ነሐሴ 23 ቀን 2018 ዓ.ም (ኢግሥኮ):- የኢትዮጵያ የግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን ዓመታዊ በዓል በተለያዩ ዝግጅቶች ነሐሴ 23 ቀን 2018 ዓ.ም በኮርፖሬሽኑ ዋና መስሪያ ቤት ተከበረ።

በዚህ ወቅት የኮርፖሬሽኑ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ወ/ሮ የሺእመቤት ነጋሽ ባደረጉት የመክፈቻ ንግግር፣ የ2018 በጀት ዓመት ኮርፖሬሽኑን ወደ ተሻለ ደረጃ የሚያሸጋግሩ መሠረቶች የተጣሉበት ዓመት መሆኑን ገልጸዋል። በተለይም በተቋሙ አሠራር፣ አደረጃጀት፣ በንብረት አስተዳደርና አያያዝ አዎንታዊ ለውጦች መደረጋቸውን አብራርተዋል።

በበጀት ዓመቱ በገቢና በትርፍ በኩል ከዕቅድ በላይ አፈጻጸም መመዝገቡን የጠቆሙት ዋና ሥራ አስፈጻሚዋ፣ አፈጻጸሙ ባለፉት ሦስት ዓመታት ከተመዘገበው አፈጻጸም የላቀ መሆኑን አስታውቀዋል።

ለዚህ ስኬት መገኘት የኮርፖሬሽኑ የሥራ አመራር ቦርድ፣ የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግስ፣ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት፣ የግብርና ሚኒስቴር፣ የኢትዮጵያ የግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢንስቲትዩት፣ የኮርፖሬሽኑ አመራሮችና ሠራተኞች፣ ደንበኞች እንዲሁም የሌሎች ባለድርሻ አካላት የተቀናጀ ርብርብ ከፍተኛ አስተዋፅኦ ማበርከቱን በመጠቆም ምስጋና አቅርበዋል።

​የሥራ አመራር ቦርድ አባል አቶ ዳንኤል ስለሺ በበኩላቸው፣ ቦርዱ ከኮርፖሬሽኑ አመራርና ሠራተኞች ጎን በመሆን ለአዎንታዊ ለውጦች መመዝገብ የድርሻውን መወጣቱን ገልጸው፣ በቀጣይም አስፈላጊው ድጋፍ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ተናግረዋል።

የመሠረታዊ ሠራተኞች ማኅበር ሊቀመንበር አቶ ብርሃኑ ደበሌ በበጀት ዓመቱ አመራሩና ሠራተኛው በመተባበር ላስመዘገቡት ውጤት ምስጋና አቅርበው፤ በቀጣይም እያንዳንዱ ሠራተኛ በተሰማራበት የሥራ ዘርፍ የሚጠበቅበትን ኃላፊነት በብቃት በመወጣት ለጋራ ስኬት እንዲሠራ ጥሪ አቅርበዋል።

​በዝግጅቱ ማጠቃለያ ላይ ለተቋሙ ውጤታማነት ከፍተኛ አስተዋፅኦ ላበረከቱ የሕዝብ ተወካዮች ም/ቤት የመንግሥት የልማት ድርጅቶች ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አባላት እንዲሁም ኮርፖሬሽኑን ለበርካታ ዓመታት አገልግለው በጡረታ ለተሰናበቱ አመራሮችና ሠራተኞች የምስጋና እና የእውቅና የምስክር ወረቀት ተሰጥቷቸዋል።

በመርሐ ግብሩ ላይ የኢትዮጵያ የግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተርና የኮርፖሬሽኑ የሥራ አመራር ቦርድ አባል ማንደፍሮ ንጉሤ (ዶ/ር)፣ የሕዝብ ተወካዮች ም/ቤት የመንግሥት የልማት ድርጅቶች ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ መለሰ መና እና የኮሚቴው አባላት እንዲሁም የኢትዮ ኢንጅነሪንግ ግሩፕ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ኮሌኔል ሸጋው ሙሉጌታ እና ሌሎች የባለድርሻ አካላት ተገኝተዋል።
###
ግብርናን ማዘመን ግባችን ነው!

የኮርፖሬሽኑ አፈጻጸም ከፍተኛ መሆኑ ተገለጸ

አዲስ አበባ፣ ነሐሴ 21 ቀን 2018 ዓ.ም (ኢግሥኮ)፦ የኢትዮጵያ የግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን የ2018 በጀት ዓመት ዕቅድ አፈጻጸም ከፍተኛ መሆኑን የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግስ (ኢኢሆ) ገለጸ።

የኮርፖሬሽኑ አፈጻጸም ነሐሴ 21 ቀን 2018 ዓ.ም በኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግስ በተገመገመበት ወቅት፣ ተቋሙ ያስመዘገበው አፈጻጸም ከፍተኛ መሆኑን የሆልዲንጉ ምክትል ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ሀብታሙ ኃይለሚካኤል አስታውቀዋል።

የኮርፖሬሽኑ አዲሱ አመራር በኃላፊነት በመሥራቱ በአጭር ጊዜ ውስጥ ለውጥ ሊያመጣ ችሏል ያሉት አቶ ሀብታሙ፣ የተቋሙን ገጽታ በመጠበቅና ልማቱን በማስቀጠል በኦፕሬሽን፣ በፋይናንስና በማኅበራዊ ኃላፊነት ያስመዘገበውን ከፍተኛ ውጤት ኢኢሆ ያደንቃል ብለዋል።

የኢትዮጵያ የግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን በ2018 በጀት ዓመት ከ438 ሺህ ኩንታል በላይ ምርጥ ዘር ያመረተ ሲሆን፣ ከ20.8 ሚሊዮን ኩንታል በላይ የአፈር ማዳበሪያ ለተጠቃሚዎች አቅርቧል።

በፋይናንስ ረገድም፣ የኮርፖሬሽኑ የ2018 በጀት ዓመት ገቢና ትርፍ ካለፉት ሦስት ዓመታት (ከ2015-2017) ጋር ሲነጻጸር ከፍተኛ ሲሆን፣ በበጀት ዓመቱ የ15.3 ቢሊዮን ብር ገቢና የ3.6 ቢሊየን ብር ትርፍ ተመዝግቧል።
               ###
ግብርናን ማዘመን ግባችን ነው!

የኮፈሌ ቅርንጫፍ ከ1.4 ቢሊዮን ብር በላይ ሽያጭ አከናወነ

አዲስ አበባ፣ ነሐሴ 14 ቀን 2018 ዓ.ም (ኢግሥኮ):- በኢትዮጵያ የግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን የኮፈሌ ቅርንጫፍ ጽ/ቤት በ2018 በጀት ዓመት ከ1.4 ቢሊዮን ብር በላይ ዋጋ ያላቸውን ዘርና የምግብ እህል ለአርሶ አደሮችና ሌሎች ተጠቃሚዎች መሸጡን ገለጸ።

​የጽ/ቤቱ ሥራ አስኪያጅ አቶ ቡሽራ መሐመድ እንደገለጹት፣ ቅርንጫፍ ጽ/ቤቱ በበጀት አመቱ ከ1.4 ቢሊየን ብር በላይ ዋጋ ያላቸውን 58 ሺህ 884 ኩንታል ምርጥ ዘርና 49 ሺህ 50 ኩንታል የምግብ እህል ለገበያ አቅርቧል።

​በተጨማሪም ቅርንጫፉ በኮፈሌ ከተማ ባለው የዘር ማበጠሪያና ማዘጋጃ ማዕከል 55 ሺህ 737 ኩንታል ዘር አበጥሮ በማዘጋጀት ለአርሶ አደሮች ማቅረቡን ሥራ አስኪያጁ አስታውቀዋል።

በሌላ በኩል በበጀት ዓመቱ በኮንትራት እርሻ በተለይም በባሌ ዞኖች በሚገኙ ሰፋፊ የመንግሥትና የባለሀብት እርሻዎች 6 ሺህ 244 ሄክታር መሬት በዘር በመሸፈን ከ155 ሺህ ኩንታል በላይ ምርት በትብብር መመረቱን አቶ ቡሽራ ተናግረዋል።

የቅርንጫፉ የዘር አቅርቦት በኮፈሌ፣ ዶዶላ፣ ገደብ አሳሳ፣ ሻሸመኔ፣ አርሲ ነገሌና በባሌ ዞን አካባቢዎች የሚገኙ አርሶ አደሮችንና ሌሎች ተጠቃሚዎችን ተደራሽ ያደርጋል።

​በ1971 ዓ.ም የተቋቋመው የኮፈሌ ቅርንጫፍ፣ ከኢትዮጵያ የግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን አንጋፋ ቅርንጫፎች መካከል አንዱ ሲሆን፣ በዋናነት በምርጥ ዘር ምርት፣ ዝግጅትና አቅርቦት ሥራ ላይ ተሰማርቶ እየሠራ ይገኛል።
              ###
ግብርናን ማዘመን ግባችን ነው!

ማስታወቂያ

የኮርፖሬሽኑ የሀዋሳ ቅርንጫፍ ዘር እያባዛ ነው

ማስታወቂያ

የኮርፖሬሽኑ አመራሮች በአለታ ወንዶ አረንጓዴ አሻራቸውን አኖሩ