የኢትዮጵያ የግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን Ethiopian Agricultural Businesses Corporation

ኮርፖሬሽኑ 46 ትራክተሮችን ለተጠቃሚዎች አስረከበ

የኢትዮጵያ የግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን (ኢግሥኮ) ከ151 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ 46 ዱዝ-ፋር (DEUTZ-FAHR) ትራክተሮችንከጣሊያንሀገርበማስመጣትለተጠቃሚዎችበሽያጭ አስረክቧል፡፡ ከ110 እስከ 180 የፈረስ ጉልበት ያላቸው እነዚህ ትራክተሮች በሽያጭ የቀረቡት ለአማራ ክልል ግብርና ቢሮ፣ ለሲዳማ ክልል እርሻ እና የተፈጥሮ ሃብት ቢሮ እንዲሁም ለእንጅባራ፣ ደብረ ብርሃን እና ጎንደር ዩኒቨርሲቲዎች፤ ለአጋርፋ ግብርና ኮሌጅ እና በእርሻ ሥራ ላይ ለተሰማሩ ባለሃብቶች ነው፡፡ ትራክተሮቹ የ2021 እና 2022 ምርት በመሆናቸው ዘመኑ የደረሰበትን ቴክኖሎጂ ከማሟላታቸው ባሻገር ለሀገራችን የአየር ንብረትና የመሬት አቀማመጥ ተስማሚ ስለመሆናቸው ተጠቃሚዎች ይመሰክራሉ፡፡ ከዚህ አኳያ ትራክተሮቹ በሀገራችን ሜካናይዝድ እርሻን ለማስፋፋት፣ ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ እና የግብርናውን ዘርፍ ለማዘመን ከፍተኛ ፋይዳ እንደሚኖራቸው ይታመናል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ ኮርፖሬሽኑ የተጨማሪ 12 ዱዝ-ፋር ትራክተሮች ግዥ የፈጸመ ሲሆን፣ ከሚቀጥለው ሳምንት ጀምሮ ሀገር ውስጥ ይደርሳሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡ በቀጣይም የአመራረት ዘዴን በቴክኖሎጂ የተደገፈ ለማድረግ ዘመናዊ፣ አስተማማኝና ጥራት ያላቸውን የእርሻ መሣሪያዎች እስከ መለዋወጫቸው ከውጭ ሀገር በማስመጣት ለተጠቃሚዎች በተመጣጣኝ ዋጋ ለማቅረብ ቅድመ ዝግጅት እየተደረገ ነው፡፡ በሌላ በኩል ኮርፖሬሽኑ ለሚያቀርባቸው ትራክተሮች ከሽያጭ በኋላ የጥገና፣ የቴክኒክ ሞያ ሥልጠና እንዲሁም መለዋወጫዎችን የማቅረብ አገልግሎቶችን ይሰጣል፡፡ እንዲሁም ከግብርና ማሳደጊያዎች ግብዓት እና መሣሪያዎች አቅርቦት በተጨማሪ ከመሬት ዝግጅት እስከ ጎተራ የሚዘልቅ የተቀናጀ የግብርና ሜካናይዜሽን አገልግሎት ተደራሽ እያደረገ ይገኛል፡፡ በተጨማሪ የእርሻና የኮንስትራክሽን መሣሪያዎች ኪራይ፣ የደረቅ ጭነት ትራንስፖርት፣ የተሽከርካሪዎች ጥገና፣ የዘር ብጠራ እና የማማከር ሥራ በኮርፖሬሽኑ የሚሰጡ ሌሎች አገልግሎቶች ናቸው፡፡ በአምስት ትላልቅ የልማት ደርጅቶች ውህደት በሚኒስትሮች ምክር ቤት ደንብ ቁጥር 368/2008 መሠረት ታህሳስ 2008 ዓ.ም የተቋቋመው የኢትዮጵያ የግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን (ኢግሥኮ) ለግብርና ምርትና ምርታማነት እድገት እና ለዘርፉ መዘመን የላቀ አስተዋጽዖ ያላቸውን ምርጥ ዘር፣ የአፈር ማዳበሪያ፣ አግሮኬሚካልና የኬሚካል መርጫ መሣሪያዎችን እንዲሁም የእርሻ መሣሪያዎችን ከነመለዋወጫቸው ለተጠቃሚዎች በተመጣጣኝ ዋጋ በማቅረብ ላይ ይገኛል።

ግብርናን ማዘመን ግባችን ነው!

“ለኮርፖሬሽኑ ምርጥ ዘር ለሚያባዙ ባለሃብቶች የምናደርገውን ድጋፍ አጠናክረን እንቀጥላለን” የኢግሥኮ ዋና ሥራ አስፈጻሚ

ከኢትዮጵያ የግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን (ኢግሥኮ) ጋር ውል ገብተው ምርጥ ዘር እያባዙ ለሚገኙ ባለሃብቶች ኮርፖሬሽኑ የሚያደርገውን ድጋፍ አጠናክሮ እንደሚቀጥል የተቋሙ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ገለጹ፡፡ ዋና ሥራ አስፈጻሚው አቶ ክፍሌ ወልደማርያም ይህን የገለጹት፣ በምስራቅ ባሌ ዞን  በኮንትራት እርሻ ለኮርፖሬሽኑ የምርጥ ዘር እያባዙ ከሚገኙ ባለሃብቶችና የባለድርሻ አካላት ጋር  በቢሾፍቱ ያቱ ሆቴል ግንቦት 28/2014 ዓ.ም. በተካሄደ የምክክር መድረክ ላይ ነው፡፡ “እናንተ ዘር የምታባዙት ለእኛ በመሆኑ ከራሳችን እርሻ ለይተን አናያችሁም” ያሉት አቶ ክፍሌ፣ ለዚህም አስፈላጊውን ድጋፍ ሁሉ ለማድረግ እና በትብብር ለመስራት ቁርጠኛ ነን ብለዋል፡፡ ባለሃብቶቹ በበኩላቸው ምርጥ ዘር የማባዛት ሥራን ከኮርፖሬሽኑ ጋር በትብብር እየሰሩና በተቋሙም ድጋፍ እየተደረገላቸው ስለመሆኑ አስታውሰው፣ በቀጣይም ድጋፉ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ያላቸውን እምነት ገልጸዋል፡፡ አክለውም በአፈር ማዳበሪያ፣ በመስራች ዘር እና አግሮኬሚካሎች አቅርቦት ላይ ያጋጠሙ ችግሮች እንዲስተካከሉ እንዲሁም የሰብል ዝርያዎች ምርታማነት እየቀነሰ ከመሆኑ ጋር ተያይዞ ከፍተኛ ምርት የሚሰጡ አዳዲስ የተሻሻሉ የሰብል ምርጥ ዘሮች እንዲቀርብላቸው ጠይቀዋል፡፡

 የኮርፖሬሽኑ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ከባለሃብቶች ለተነሱ ጥያቄዎች በሰጡት ምላሽ፣ የተጠየቁ የግብርና ግብዓቶችን በቀጣይ ጊዜያት እንደሚያቀርቡ ተናግረዋል። በኮርፖሬሽኑ የኦፕሬሽን ዐቢይ ዘርፍ ምክትል ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ፈለቀ ገዛኸኝ በመድረኩ ባቀረቡት ገለጻ፣ ኮርፖሬሽኑ በሀገር አቀፍ ደረጃ ከ25 እስከ 30 በመቶ የሚሆነውን የምርጥ ዘር አቅርቦት እየሸፈነ እንደሚገኝ ጠቁመው፣ ከዚህ ውስጥ ኮርፖሬሽኑ አብዛኛውን ዘር በሰፋፊ የመንግሥት እና ባለሃብቶች እርሻዎች እንዲሁም በአርሶ አደር ማሳ ላይ በትብብር በማምረት ለተጠቃሚዎች እንደሚያቀርብ አስታውቀዋል፡፡ ከዚህ አኳያ በዘንድሮ የሰብል ዘመን ኮርፖሬሽኑ ከ36 ሚሊዮን ብር በላይ ዋጋ ያለው ምርጥ ዘር በብድር ለባለሃብቶች መስጠቱን እንዲሁም የሞያና ሌሎች ድጋፎችን ማድረጉን በኮርፖሬሽኑ የኢትዮጵያ ምርጥ ዘርና ደን ውጤቶች አቅርቦት ዘርፍ ሥራ አስፈጻሚ አቶ ዘነበ ወልደሥላሴ ተናግረዋል። የኮፈሌ ቅ/ጽ/ቤት ሓላፊ አቶ ቡሽራ መሐመድ በበኩላቸው፣ ቅርንጫፉ ከምርጥ ዘር አባዥ ባለሃብቶች ጋር በመተባበር በመጪው የመኸር ወቅት 5 ሺህ ሄክታር የሚጠጋ መሬት በዘር በመሸፈን ከ131 ሺህ ኩንታል በላይ ምርጥ ዘር ለማምረት አቅዶ አየሰራ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ኮርፖሬሽኑ በኮንትራት እርሻ በተለያዩ አካባቢዎች በባለሃብቶች መሬት ከሚያባዛው ምርጥ ዘር ውስጥ  በምስራቅ ባሌ ዞን የሚያባዛው ከፍተኛ ድርሻ እንዳለው አቶ ቡሽራ ጠቁመዋል፡፡ በውይይት መድረኩ ላይ የተገኙት የምስራቅ ባሌ ዞን ምክትል ዋና አስተዳዳሪ አቶ መሐመድ እስማኤል ባስተላለፉት መልእክት፣ ኮርፖሬሽኑ በዞኑ ለሚያደርገው የግብርና ልማት በጋራ ከማቀድ ጀምሮ ተገቢውን ድጋፍ እንደሚያደርጉ አስታውቀው፣ በዞኑ ያለውን የመስኖ ልማት በመጠቀም ለቆላማ አካባቢዎች ተስማሚ የሆኑ ምርጥ ዘር የማባዛት ሥራ ላይ ትኩረት ማድረግ እንደሚገባ አቅጣጫ አመላክተዋል። በመድረኩ ስለ ምርጥ ዘር አመራረት፣ አዘገጃጀትና ሥርጭት፤ የዘር ጥራት ቁጥጥር፣ መርሆዎችና ሂደት እንዲሁም የሀገሪቱ የምርጥ ዘር ፖሊሲ፣ ህግና ደንብን አስመልከቶ በባለሞያዎች የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥልጠና ተሰጥቷል፡፡ የኮፈሌ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ባዘጋጀው በዚህ የግማሽ ቀን የውይይት መድረክ ላይ የኮርፖሬሽኑ አመራሮችና ባለሞያዎች፤ የምስራቅ ባሌ ዞን ምክትል ዋና አስተዳዳሪ፣ የዞኑ የግብርና እና ኢንቨስትመንት ጽ/ቤት ሓላፊዎች፤ በምርጥ ዘር ብዜት የተሰማሩ ድርጅቶች እና ማህበራት እንዲሁም የአርዳይታ እና አጋርፋ የግብርና ቴክኒክና ሞያ ማሠልጠኛ ኮሌጆች ተገኝተዋል፡፡ በመድረኩ ማጠቃለያም በ2013/14 የምርት ዘመን ከኮርፖሬሽኑ ጋር በመተባበር በምስራቅ ባሌ ዞን በኮንትራት እርሻ በምርጥ ዘር ብዜት የላቀ አስተዋጽዖ ላበረከቱ የዘር አባዦችና የባለድርሻ አካላት የምስጋናና የእውቅና የምስክር ወረቀት ተሰጥቶአቸዋል። የኢትዮጵያ የግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን በራሱ እርሻዎች፣ በሰፋፊ የመንግሥት እና ባለሃብት እርሻዎች እንዲሁም በአርሶ አደር ማሳ ላይ ምርጥ ዘርን በጥራት እና በብዛት በማባዛት ለተጠቃሚዎች እያሰራጨ የሚገኝ የመንግሥት የልማት ድርጅት ነው፡፡

ግብርናን ማዘመን ግባችን ነው!

የደን ውጤት ምርቶችን ወደ ውጭ በመላክ ከ900 ሺህ ዶላር በላይ ገቢ ተገኝቷል

ነሐሴ 4/2013 (ኢዜአ) የደን ውጤት የሆኑ ምርቶችን ወደ ውጭ በመላክ ከ900 ሺህ ዶላር በላይ መገኘቱን የኢትዮጵያ የግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን ገለፀ።

የኮርፖሬሽኑ ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ ክፍሌ ወልደማርያም የተቋሙን የ2013 በጀት ዓመት ስራ አፈፃፀም አስመልክተው መግለጫ ሰጥተዋል።

በመግለጫቸው የምርጥ ዘር፣ የደን ውጤቶችና የግብርና ምርት ማሳደጊያ አቅርቦቶችን ጨምሮ የእርሻ መሳሪያዎች አቅርቦትና የሜካናይዜሽን አገልግሎትን ከማስፋት አኳያ የተሰሩ ስራዎችን አብራርተዋል።

የደን ውጤቶች የሆኑትን እንደ ሙጫ፣ እጣን፣ ከርቤ እና አበክድ ምርቶችን ወደ ውጭ በመላክ በበጀት ዓመቱ ከ900 ሺህ በላይ ዶላር ገቢ መገኘቱን ጠቅሰዋል።

ገቢው የተገኘው የደን ውጤቶችን ለማምረት በማኅበር ከተደራጁ ወጣቶች ከተሰባሰበው ከሁለት ሺህ ኩንታል በላይ ምርት እንደሆነም ገልጸዋል።

ዋና ስራ አስፈጻሚው በበጀት ዓመቱ ከ13 ሺህ ሄክታር በሚልቅ መሬት ከ284 ሺህ ኩንታል በላይ ምርጥ ዘር ማምረት እንደተቻለ ገልጸዋል።

በበጀት ዓመቱ ከ172 ሺህ 395 ኩንታል ምርጥ ዘር ከ617 ሚሊዮን ብር በላይ ሽያጭ መከናወኑን አክለዋል።

በሌላ በኩል በግብርና ምርት ማሳደጊያ አቅርቦት ከ600 ሚሊዮን ዶላር በላይ ወጪ ከውጭ አገር የአፈር ማዳበሪያ፣ ፀረ አረም እና ተባይ ኬሚካሎች ተገዝተው ለተጠቃሚዎች መሰራጨታቸውን ተናግረዋል።

የዓለም ገበያ የማዳበሪያ ዋጋ ጭማሪ አርሶ አደሩን እንዳይጫን ኮርፕሬሽኑ ከ60 ሚሊዮን ብር በላይ ኪሳራ በመውሰድና መንግሥት በበኩሉ ከ4 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር በላይ የትራንስፖርት ወጪ በመሸፈን ተሰራጭቷል ብለዋል።

የእርሻ መሳሪያዎች አቅርቦትና  የሜካናይዜሽን አገልግሎትን ከማስፋት አንፃርም ከ73 ሚሊዮን ብር በላይ ዋጋ ያላቸው የእርሻ መሳሪያዎችና መለዋወጫዎች ለተጠቃሚዎች ቀርበዋል ብለዋል።

አቶ ክፍሌ አያይዘውም በ2014 በጀት ዓመት ምርጥ ዘር የማባዛትና የማሰራጨት ስራ በትኩረት እንደሚከናወን ጠቁመዋል።

በአገሪቷ ሁሉም አከባቢዎች የሚገኙ የኮርፖሬሽኑ መሬቶች ፆም እንዳያድሩ እየተሰራ መሆኑንም አክለዋል። 

የግብርና ግብዓቶች አቅርቦትን ለማሳደግና ተደራሽ ለማድረግ፣ የተቀናጀ የሜካናይዜሽን አገልግሎት ለማስፋትና ከክልሎች የተገኙ የእርሻ መሬቶችን ለማልማት እንቅስቃሴ መጀመሩንም ነው የተናገሩት። የኢትዮጵያ ግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን የግብርና ምርትና ምርታማነትን የሚያሳድጉ ቴክኖሎጂዎችን ለአርሶና አርብቶ አደሩ ተደራሽ በማድረግ የአገሪቷን የምጣኔ ሀብት እድገት የማገዝ ዓላማ አንግቦ የሚሰራ ተቋም ነው

የግብርና ሚኒስትሩና የኮርፖሬሽኑ የሥራ አመራር ቦርድ የአሰላ ቅርንጫፍ ጎንዴ ኢተያ እርሻ ጣቢያዎችን ጎበኙ

የግብርና ሚኒስትሩና የኢትዮጵያ የግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን የሥራ አመራር ቦርድ የአሰላ ቅርንጫፍ ጎንዴ ኢተያ እርሻ ጣቢያዎችን ነሐሴ 16/2013 ዓ.ም ጎበኙ።

በጉብኝቱ ወቅት የተገኙት የኢፌዲሪ የግብርና ሚኒስቴር ሚኒስትር አቶ ዑመር ሁሴን፣ የኢትዮጵያ የግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን የሥራ አመራር ቦርድ ሰብሳቢ ዶክተር ግርማ አመንቴ እና የኮርፖሬሽኑ የቦርድ አባላት አሰላ ቅርንጫፍ ጎንዴ ኢተያ እርሻ ጣቢያዎች ላይ የተዘሩ የጤፍ፣ ስንዴ፣ ባቄላ፣ ጎመን፣ ተልባ፣ ሽምብራና በቆሎ የሰብል ዘሮችን ተዘዋውረው ተመልክተዋል።

 በተጨማሪም የአሰላ ቅርንጫፍ የምርጥ ዘር መጋዘንና የዘር ማበጠሪያ (ማዘጋጃ) ማሽን ጎብኝተዋል።

 ከጉብኝቱ በኋላ በተደረገ ውይይት አስተያየታቸውን የሰጡት የኮርፖሬሽኑ የሥራ አመራር ቦርድ ሰብሳቢ ዶክተር ግርማ አመንቴ በተመለከቱት የልማት ሥራ መደሰታቸውን ገልጸዋል።

አክለውም ኮርፖሬሽኑ ለምርጥ ዘር ማባዣ የሚውል ተጨማሪ መሬት ለማግኘት የሚያደርገውን ጥረት አጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት ጠቁመው፣ በተለይም የአርሶ አደሩን ማሳ ለዘር ማባዣነት ለመጠቀም የጋራ ተጠቃሚነትን መሰረት ያደረገ የኮንትራት እርሻ የአሠራር ስምምነት (contractual farming system) መተግበር እንዳለበት አስታውቀዋል።

 በዚህ የአሠራር ስምምነት አርሶ አደሩ የእርሻ መሬቱን ተጠቅሞ ኮርፖሬሽኑ የሚያቀርብለትን ምርጥ ዘር ካባዛ በኋላ ኮርፖሬሽኑ ምርቱን መልሶ ስለሚገዛው የበርካታ ሰብል ዝርያዎችን ዘር በአርሶ አደሩ ማሳ ላይ ማባዛት እንደሚቻል አስረድተዋል።

በአስተያየታቸው ማጠቃለያም የግብርናውን ዘርፍ ለማዘመን ኮርፖሬሽኑ የተሰጠውን ተልዕኮ ይበልጥ መወጣት እንዲችል ከአርሶ አደር ጋር በሚደረግ የኮንትራት እርሻ ስምምነት፣ በአፈር ማዳበሪያ ግብይትና ፋይናንስ ሥርዓት ፖሊሲ፣ በሚወገድ ማዳበሪያ፣ በፋይናንስ እና አፋጣኝ መፍትሔ በሚያስፈልጋቸው ሌሎች ጉዳዮች ዙሪያ የግብርና ሚኒስቴር እገዛ እንደሚያስፈልግ ተናግረዋል።

 የግብርና ሚኒስትሩ አቶ ዑመር ሁሴን በበኩላቸው በተመለከቱት ሁሉ መደሰታቸውን ገልጸው፣ ኮርፖሬሽኑ የዘር ብዜት ሥራውን ይበልጥ ማስፋትና ማሳደግ እንደሚጠበቅበት ተናግረዋል።

አያይዘውም ኮርፖሬሽኑ ያጋጠሙትን ተግዳሮቶች ለመፍታት የተቋሙ የሥራ አመራር ቦርድ ጉዳዩ የሚመለከታቸው የባለድርሻ አካላት የሚሳተፉበት የውይይት መድረክ እንዲያዘጋጅ ጠይቀዋል።

 ይህን በተመለከተም የኮርፖሬሽኑ የቦርድ ሰብሳቢ ዶክተር ግርማ አመንቴ በቅርቡ አንድ የምክክር መድረክ እንዲዘጋጅ ለኮርፖሬሽኑ ማኔጅመንት የሥራ መመሪያ ሰጥተዋል።  በኢትዮጵያ የግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን የአሰላ ቅርንጫፍ ጎንዴ ኢተያ እርሻ ጣቢያዎች በ2013/14 የሰብል ዘመን የመኸር ወቅት በ389 ሄክታር መሬት ላይ በ10 ሰብሎች 36 የተለያዩ ቅድመ መስራች እና መስራች ዝርያዎች ተዘርተዋል።

ኮርፖሬሽኑን ወደ ተሻለ የእድገት ምዕራፍ የሚያሸጋግሩ አዳዲስ ሃሳቦችን ማፍለቅ እንደሚገባ ተገለጸ

“ኮርፖሬሽኑ ካለው አፈጻጸምና ልምድ አንጻር በ2014 በጀት ዓመት የተሻለ ውጤት እንደሚያስመዘግብ ተስፋ አደርጋለሁ” የኮርፖሬሽኑ የሥራ አመራር ቦርድ ሰብሳቢ

የኢትዮጵያ የግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽንን ወደ ተሻለ የእድገት ምዕራፍ የሚያሸጋግሩ አዳዲስ ሃሳቦችን ማፍለቅ እንደሚገባ የኮርፖሬሽኑ የሥራ አመራር ቦርድ ሰብሳቢ ገለጹ፡፡

የቦርድ ሰብሳቢው ዶክተር ግርማ አመንቴ ይህንን የገለጹት ነሐሴ 22/2013 ዓ.ም በተካሄደ የኮርፖሬሽኑ የሠራተኞች አመታዊ ስብሰባ ላይ ነው፡፡

በስብሰባው ወቅት የተቋሙ የ2013 በጀት ዓመት አፈጻጸምና የ2014 በጀት ዓመት ዕቅድ ቀርቦ ውይይቱን የቦርድ ሰብሳቢው መርተውታል፡፡

በ2013 በጀት ዓመት የተገኘውን አበረታች ውጤት ያደነቁት ሰብሳቢው፣ እያንዳንዱ ሠራተኛ እኔ ሰርቼ ያመጣሁት ውጤት ነው የሚል አስተሳሰብ ማዳበር እንዳለበት አስረድተዋል፡፡

ይሁንና በአንዱ ትክሻ ሌላው ቁጭ ብሎ ሳይሰራ መጠቀም እንደሌለበትም አስገንዝበዋል፡፡ ከሥራ ክፍል አኳያም አንዱ ያተረፈውን ሌላው እየበላ ኮርፖሬሽኑን ለኪሳራ መዳረግ እንደሌለበት አሳስበዋል፡፡

ኮርፖሬሽኑ ባለው የእርሻ መሬት ሁለቴና ሦስቴ ማምረት እንደሚጠበቅበት የገለጹት ዶክተር ግርማ፣ ከዚህ ባሻገር ከክልሎች ጋር በቅርበት በመነጋገርና በመስራት ተጨማሪ አዳዲስ የእርሻ መሬቶችን ማፈላለግና ማልማት እንደሚያስፈልግ ጠቁመዋል፡፡

የኮርፖሬሽኑን የ2014 በጀት ዓመት ዕቅድ አስመልክተው ሲናገሩም ድርጅቱ ካለው አፈጻጸምና ልምድ አንጻር በበጀት ዓመቱ የተሻለ ውጤት እንደሚያስመዘግብ ተስፋ አደርጋለሁ ብለዋል፡፡ ለዕቅዱ ስኬትም እንደምንግዜውም ሁሉ የቦርዱ ድጋፍና ክትትል እንደማይለይ በራሳቸውና በሥራ አመራር ቦርዱ ስም አረጋግጠዋል፡፡

የእለቱን ስብሰባ በንግግር የከፈቱት የኮርፖሬሽኑ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ክፍሌ ወልደማርያም በበኩላቸው፣ ኮርፖሬሽኑ ከተቋቋመበት ከ2008 ዓ.ም ጀምሮ በማኔጅመንቱና በሠራተኛው ከፍተኛ ጥረት እንዲሁም በተቋሙ የሥራ አመራር ቦርድ እና በመንግሥት የልማት ድርጅቶች ይዞታና አስተዳደር ኤጀንሲ ሁለገብ ድጋፍ በየአመቱ ትርፋማነቱን አስጠብቆ መዝለቁን ተናግረዋል፡፡

“በተለይም በ2013 በጀት ዓመት በኮሮና ቫይረስ በሽታ ወረርሽኝ፣ በጸጥታ ችግሮችና በውጭ ምንዛሪ እጥረት ሳቢያ ባጋጠመን ፈታኝ ሁኔታ ውስጥ ሆነን የተገኘ ትርፍ አፈጻጸም ካለፉት አራት ዓመታት አማካይ እና ከ2012 በጀት አመት አፈጻጸም ጋር ሲነጻጸር በቅደም ተከተል 42% እና 8% እድገት አሳይቷል” ብለዋል፡፡

ለውጤቱ መሳካትም የበኩላቸውን ድጋፍ ላደረጉ የኮርፖሬሽኑ የሥራ አመራር ቦርድ አባላት፣ የመንግሥት የልማት ድርጅቶች ይዞታና አስተዳደር ኤጀንሲ እና በገንዘብ ሚኒስቴር የመንግሥት ልማት ድርጅቶች ክትትልና ድጋፍ ዳይሬክቶሬት ምስጋና አቅርበዋል፡፡

በተመሳሳይ የተቋሙ የመሰረታዊ የሠራተኛ ማኅበር፣ መላው የሥራ ኃላፊዎችና ሠራተኞች ለኮርፖሬሽኑ ዕቅድ መሳካት ላበረከቱት አስተዋጽዖ በኮርፖሬሽኑ እና በራሳቸው ስም አመስግነዋል፡፡ በስብሰባው ላይ የሥራ አመራር ቦርድ አባላት፣ የመንግሥት የልማት ድርጅቶች ይዞታና አስተዳደር ኤጀንሲ እና የገንዘብ ሚኒስቴር የሥራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል፡፡