የኢትዮጵያ የግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን Ethiopian Agricultural Businesses Corporation

በኮርፖሬሽኑ የባህር ዳር ቅርንጫፍ ጽ/ቤት ከ859 ሚሊዮን ብር በላይ ዋጋ ያላቸውን የግብርና ምርት ማሳደጊያ ግብዓቶችን ማሰራጨቱን ገለጸ

አቶ እርቄ ገላው
በኢትዮጵያ የግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን የባህር ዳር ቅርንጫፍ ጽ/ቤት ኃላፊ

አዲስ አበባ፣ ጥር 29 ቀን 2015 ዓ.ም (ኢግሥኮ)፡- በኢትዮጵያ የግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን የባህር ዳር ቅርንጫፍ ጽ/ቤት ከ859 ሚሊዮን ብር በላይ ዋጋ ያላቸውን የግብርና ምርት ማሳደጊያ ግብዓቶችን ለተጠቃሚዎች ማሰራጨቱን አስታወቀ፡፡
ቅርንጫፍ ጽ/ቤቱ የ2015 በጀት ዓመት የሰባት ወራት የሥራ አፈጻጸሙን አስመልክቶ ለኮርፖሬት ኮሚዩኒኬሽን የሥራ ክፍል በላከው መግለጫ እንዳስታወቀው፣ የቅባት እህሎችን ዘር ወደ ውጭ ሀገራት በመላክ የውጭ ምንዛሬን ለማስገኘት እየተንቀሳቀሰ ሲሆን፣ በተለይም አኩሪ አተር ላይ በትኩረት እየሰራ ይገኛል። እስካሁንም 6 ሺህ 880 ኩንታል አኩሪ አተር መሰብሰቡን አስታውቋል፡፡
የመስኖ ልማትን ታሳቢ በማድረግም 2 ሺህ 100 ኩንታል ዘር መዘጋጀቱንና የተዘጋጀው ዘርም በውጭ ሀገር የዘር ጥራት ተቆጣጣሪ አካላት ጥራቱ እንዲረጋገጥ መደረጉን ገልጿል፡፡
ቅርንጫፍ ጽ/ቤቱ ባለፉት ሰባት ወራት ከ859 ሚሊዮን ብር በላይ ዋጋ ያላቸውን ምርጥ ዘር፣ የአፈር ማዳበሪያ እና አግሮኬሚካሎችን ለጎንደር፣ ጎጃም፣ አዊ እና ሌሎችም አካባቢዎች ተደራሽ አድርጓል፡፡
በዚህም 7 ሺህ 356 ኩንታል ምርጥ ዘር፣ 282 ሺህ 583 ኩንታል የአፈር ማዳበሪያ፣ 13 ሺህ 59 ሊትር እና 500 ኪ.ግ ዱቄት አግሮኬሚካል ለምዕራብ አማራ አካባቢዎች ማሰራጨቱን በመግለጫው ጠቁሟል፡፡
በሌላ በኩል ቅርንጫፍ ጽ/ቤቱ በ2014/15 የመኸር ወቅት በመንግሥት ዩኒቨርሲቲ፣ በሰፋፊ ባለሀብት እርሻዎች እና በአርሶ አደር ማሳዎች በ1 ሺህ 490 ሄክታር መሬት የበቆሎ፣ ስንዴ እና አኩሪ አተር ሰብል ምርጥ ዘሮችን ማባዛቱን እና እስከ ጥር 26 ቀን 2015 ዓ.ም ድረስ 18 ሺህ 334 ኩንታል ዘር ተሰብስቦ ወደ መጋዘን መግባቱን አስታውቋል፡፡
የዘር ብዜት ሥራን ከ882 አርሶ አደሮች፣ ከአንድ የመንግሥት ዩኒቨርሲቲ እና ከ13 የግል ባለሀብቶች ጋር በጋራ ማከናወኑንም በመግለጫው አንስቷል፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ ከ20 በላይ የተለያዩ ዝርያዎችን የማስተዋወቅ ሰርቶ ማሳያ መካሄዱን ከጽ/ቤቱ መግለጫ ለመረዳት ተችሏል፡፡

ኮርፖሬሽኑ በዘንድሮ የመኸር ምርት ዘመን እስካሁን 195 ሺህ ኩንታል የተሻሻለ የምርጥ ዘር መሰብሰቡን ገለጸ

አዲስ አበባ (ኢዜአ) ጥር 20 ቀን 2015፡- በ2014/15 የመኸር ምርት ዘመን እስካሁን 195 ሺህ ኩንታል የተሻሻለ ምርጥ ዘር መሰብሰቡን የኢትዮጵያ ግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን ገለጸ።

ኮርፖሬሽኑ ለኢዜአ በላከው መግለጫ እንዳስታወቀው፣ በ2014/15 የመኸር የምርት ዘመን ምርት ለመሰብሰብ በያዘው ዕቅድ መሰረት የመሰብሰብ ሥራውን እያከናወነ መሆኑን አስታውቋል።

በምርት ዘመኑ 338 ሺህ ኩንታል ለመሰብሰብ ዕቅድ መያዙን ጠቅሶ፣ እስካሁን 195 ሺህ ኩንታል በመሰብሰብ እያጓጓዘ መሆኑን ገልጿል።

ኮርፖሬሽኑ በራሱና በኮንትራት የምርጥ ዘር ልማት መሸፈን ከቻለው ከ15 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት የደረሱ ሰብሎችን በመሰብሰብ ወደ መጋዘኖች እያስገባ መሆኑንም ጠቁሟል።

በዚህም በኮፈሌ ቅርንጫፍ በምዕራብ አርሲ እና በባሌ ዞኖች በግብርና ኮሌጆች እና በሰፋፊ የግል ባለሀብት እርሻ በ5 ሺህ 427 ሄክታር መሬት ላይ ያባዛውን ዘር መሰብሰቡን ገልጿል።

በኮርፖሬሽኑ የኮፈሌ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ሥራ አስኪያጅ አቶ ቡሹራ መሐመድ፣ ከአርዳይታና አጋርፋ የግብርና ኮሌጆች በተጨማሪ በባሌ ዞኖች በባለሀብቶች እርሻ ሦስት የገብስና 10 ዓይነት የስንዴ ዝርያዎችን በማባዛት የደረሱ ሰብሎችን በመሰብሰብ የማጓጓዝ ሥራ እየተካሄደ ነው ብለዋል።

እስከ ጥር 16 ቀን 2015 ዓ.ም ድረስ ምርት የመሰብሰብ ሥራ 50 በመቶ መከናወኑን እና 52 ሺህ ኩንታል ምርት ተረክበው ወደ ኮርፖሬሽኑ መጋዘኖች መጓጓዛቸውን ገልጸዋል።

በቅርንጫፍ ጽህፈት ቤቱ የዘር ጥራት ክትትልና ቁጥጥር ቡድን መሪ አቶ ጋሩማ ገመዳ፣ የምርት ጥራትን ለማስጠበቅ ቁጥጥርና ክትትል በማድረግ የምርት መሰብሰብ ሥራ እየተፋጠነ ይገኛል ብለዋል።

በምርጥ ዘር ብዜት በእርሻ ኢንቨስትመንት የተሰማሩ ባለሀብቶችም፣ የአርሶ አደሩ ምርታማነትን በማሳደግ በቂ የምርጥ ዘር አቅርቦት እንዲኖር ለማድረግ ጥራቱን የጠበቀ ምርት እያቀረቡ መሆኑን ገልጸዋል።

በሌላ በኩል ኮርፖሬሽኑ በተቀናጀ የግብርና ሜካናይዜሽን አገልግሎት የአርሶ አደሮች፣ የመንግሥት የልማት ድርጅቶች እና የግል ባለሀብቶችን የምርጥ ዘር ሰብል በተመጣጣኝ ዋጋ የመሰብሰብና የማጓጓዝ አገልግሎት እየሰጠ መሆኑን ለኢዜአ በላከው መግለጫ ላይ ጠቅሷል።

በዚህም መሰረት እስከ ጥር 17 ድረስ ለአርሶ አደሮች፣ ለልማት ድርጅቶችና ባለሀብቶች 146 ሺህ ኩንታል ምርት መሰብሰቡን አስታውቋል። ኮርፖሬሽኑ በተለያዩ አካባቢዎች ባሉት የራሱ እና የኮንትራት እርሻዎች የ21 የሰብል ዓይነቶች 70 ዝርያዎችን በማባዛትና በማዘጋጀት ለአርሶ አደሮች እያቀረበ እንደሚገኝም ተጠቁሟል።

ኮርፖሬሽኑ ከ103 ሺህ ኩንታል በላይ የአርሶ አደሮችን እና የሌሎች ምርጥ ዘር አባዥዎችን ምርት በመሰብሰብ አስረከበ

አዲስ አበባ፣ ታህሳስ 14/2015 ዓ.ም (ኢግሥኮ) ፡- የኢትዮጵያ የግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን (ኢግሥኮ) የአርሶ አደሮች፣ የባለሃብቶች እና የመንግሥት  ተቋማት ምርጥ ዘር አባዥዎችን የደረሱ ሰብሎች በተመጣጣኝ ዋጋ በመሰብሰብ አስረከበ፡፡

በኮርፖሬሽኑ የእርሻ መሣሪያዎችና ሜካናይዜሽን አገልግሎት ዘርፍ ሥራ አስፈጻሚ አቶ መንግሥቱ ክፍሌ እንደተናገሩት፣ ኮርፖሬሽኑ እስከ ታህሳስ 12 ቀን 2015 ዓ.ም ድረስ 90 ሺህ ኩንታል ምርት ለመሰብሰብ አቅዶ ከ103 ሺህ ኩንታል በላይ የደረሰ ሰብል በመሰብሰብ ለደንበኞቹ አስረክቧል፡፡

በዋናነት ስንዴ፣ ገብስ እና ጎመን ዘር በኮምባይን ሀርቨስተር አጭደን፣ ወቅተን እና አጓጉዘን አስረክበናል ያሉት አቶ መንግሥቱ፣ ለኦሮሚያ ክልል ምርጥ ዘር ድርጅት፣ ለአየሁ እርሻ ልማት፣ ለአርሶ አደሮች እና ለኮርፖሬሽኑ ምርጥ ዘር ማባዣዎች አገልግሎቱ መሰጠቱን ገልጸዋል፡፡

አክለውም የደረሱ ሰብሎች ሙሉ በሙሉ ተሰብስበው ጎተራ እስኪገቡ ድረስ የምርት መሰብሰቡን ሥራ እንደሚቀጥሉ አስታውቀው፣  በአጠቃላይ በዚህ ዓመት ለአርሶ አደሮች እና ሌሎች የሜካናይዜሽን አገልግሎት ፈላጊዎች 261 ሺህ ኩንታል ምርት ለመሰብሰብ እየሰሩ መሆኑን ተናግረዋል።

አገልግሎቱ በ13 አጭዶ መውቂያ መሣሪያዎች እንዲሁም ምርትን ወደ አውድማ እና ጎተራ በሚያጓጉዙ 10 ገልባጭ ተሽከርካሪዎች በመታገዝ እየተሰጠ መሆኑንም አመልክተዋል።

የምርት መሰብሰብ አገልግሎቱ በአርሲ፣ ባሌ፣ ሸዋ እና ጎጃም አካባቢዎች በስፋት እየተሰጠ መሆኑን የጠቆሙት አቶ መንግሥቱ፣ የምርት መሰብሰብ ሥራው ተረፈ ምርትን ለእንስሳት መኖ እንዲሆን በሚያስችል መልኩ በጥራት እየተከናወነ መሆኑን አብራርተዋል፡፡

በሌላ በኩል ኮርፖሬሽኑ ምርት ከመሰብሰብ ሥራ ጎን ለጎን በደንበኞች ጥያቄ መሰረት የእርሻ መሬት እያዘጋጀ ነው ያሉት አቶ መንግሥቱ፣ በዚህ ረገድ በዳውሮ ዞን ዴሳ ወረዳ የቅባት እህሎችን በማምረት ለውጭ ገበያ ለማቅረብ ለተሰማራ ልማታዊ ባለሃብት እየተዘጋጀ የሚገኘው 1 ሺህ ሄክታር የእርሻ መሬት ይጠቀሳል ብለዋል፡፡

አያይዘውም እስከ ህዳር 12/2015 ዓ.ም ድረስ 130 ሄክታር የሚሆን መሬት ለእርሻ በሚመች መልኩ መዘጋጀቱን ጠቁመዋል፡፡

በተመሳሳይ የእርሻ መሣሪያዎችና ሜካናይዜሽን አገልግሎት ዘርፍ በኮርፖሬሽኑ የታማሻሎ ምርጥ ዘር ማባዣ እርሻ ልማት 300 ሄክታር መሬት በማዘጋጀት ላይ እንደሚገኝ ገልጸዋል፡፡

የማሳ ዝግጅትን በተመለከተም የኢትዮ አግሪ ሴፍት አየሁ እርሻ ልማት 2 ሺህ 500 ሄክታር መሬት ለማልማት ውል መገባቱን ያስታወቁት አቶ መንግሥቱ፣ የእርሻ መሣሪያዎችን የማጓጓዝ እና የማሰማራት ሥራ እየተከናወነ በመሆኑ በቅርቡ ሥራው እንደሚጀመር ተናግረዋል፡፡

የምርት መሰብሰብ ሥራን እና ሌሎች ውል የተገባባቸውን የግብርና ሜካናይዜሽን አገልግሎቶች በብቃት እንዲፈጸሙ ለማስቻል በአመራር ደረጃ በመስክ ተገኝቶ ሠራተኞችን በማበረታታት የተሻለ የሥራ ተነሳሽነት መፍጠር እንደተቻለም ገልጸዋል።

ግብርናን ለማዘመን የሜካናይዜሽን አገልግሎትን በስፋት ተደራሽ ማድረግ ይገባል የሚሉት አቶ መንግሥቱ፣ ከዚህ አኳያም ኮርፖሬሽኑ በግንባታ ላይ የሚገኘውን የቦንጋ የተቀናጀ የግብርና ግብዓትና የሜካናይዜሽን አገልግሎት መስጫ ማዕከልን ጨምሮ ሌሎች ተጨማሪ አዳዲስ ማዕከላትን በተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች ለማቋቋም እየሰራ ይገኛል ብለዋል፡፡ የኢትዮጵያ የግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን ከሚሰጣቸው በርካታ አገልግሎቶች ውስጥ ከመሬት ዝግጅት እስከ ጎተራ የሚዘልቅ የተቀናጀ የግብርና ሜካናይዜሽን አገልግሎት ተጠቃሽ ሲሆን፣ ተቋሙ ይህን አገልግሎት በመስጠት ለምርትና ምርታማነት እድገት እና ግብርናን ለማዘመን በሚደረገው ሀገራዊ እንቅስቃሴ የበኩሉን ድርሻ በመወጣት ላይ ይገኛል፡፡