የኢትዮጵያ የግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን Ethiopian Agricultural Businesses Corporation

ኮርፖሬሽኑ በአፈር ማዳበሪያ ግዥ፣ አቅርቦትና ሥርጭት መሳለጥ ለአበረከተው የጎላ አስተዋጽዖ ተሸለመ

አቶ ሰለሞን ገብሬ
የግብርና ምርት ማሳደጊያዎች አቅርቦት ዘርፍ ሥራ አስፈጻሚ

ለመስኖ እርሻ የሚውል የአፈር ማዳበሪያ የግዥ ሂደት ተጀመረ

Ethiopian Investment Holdings’ CEO congratulates EABC staff on their successful achievements of 2016 fiscal year

“ኮርፖሬሽኑ በ2016 በጀት ዓመት ከፍተኛ ውጤት በማስመዝገቡ እንኳን ደስ ያላችሁ” የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግስ ዋና ሥራ አስፈጻሚ

“ተቋሙ የሀገሪቱ የኢኮኖሚ ዋልታ በመሆኑ ቦርዱ የሚጠበቅበትን ሁሉ ያደርጋል” የኮርፖሬሽኑ የሥራ አመራር ቦርድ አባል

በ2016 እቅድ አፈጻጸም እና በ2017 እቅድ ዙሪያ ውይይት ተደረገ

የኮርፖሬሽኑ የ2016 በጀት ዓመት ዕቅድ አፈጻጸም ጥሩ መሆኑን የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግስ ገለጸ

የኮርፖሬሽኑ የሥራ ኃላፊዎች እና ሠራተኞች አረንጓዴ ሻራቸውን አኖሩ

5 ሚሊዮን ኩንታል የአፈር ማዳበሪያ ወደ አገር ውስጥ ገብቷል – ዶክተር ግርማ አመንቴ

(አዲስ አበባ፣ ጥር 10 ቀን 2016 ዓ.ም፣ ግብርና ሚኒስቴር) የግብርና ሚኒስትሩ ዶ/ር ግርማ አመንቴ እና የትራንስፖርትና ሎጅስቲክስ ሚኒስትሩ ዶ/ር ዓለሙ ስሜ በ2016/17 ምርት ዘመን የአፈር ማደበሪያ አገባብ ዕቅድ ክንውን ላይ የጋራ መግለጫ ሰጥተዋል፡፡ በተያዘው የምርት ዘመን የግብርና ሚኒስቴር 23 ሚሊዮን ኩንታል የአፈር ማዳበሪያ ለመግዛት አቅዶ ከክልሎች በተሰበሰበው የአፈር ማዳበሪያ ፍላጎት መሰረት 19.4 ሚሊዮን ኩንታል የአፈር ማዳበሪያ ለመግዛት 930 ሚሊዮን ዶላር ወጪ ተድርጎ ግዥ እየተፈጸመ መሆኑን ዶ/ር ግርማ አመንቴ ተናግረዋል፡፡ ግዥ ከተፈፀመው የአፈር ማዳበሪያ ውስጥም 5 ሚሊዮን ኩንታል የአፈር ማዳበሪያ ወደ አገር ውስጥ ገብቷል ብለዋል ሚኒስትሩ፡፡ በምርት ዘመኑም ከሚገዛው የአፈር ማዳበሪያ ውስጥ 25 በመቶው ለመስኖ ስንዴ ልማት፣ 20 በመቶው ለበልግ እርሻ ስራ እንዲሁም ቀሪው 55 በመቶ ለመኸር እርሻ ጥቅም ላይ እንደሚውል አብራርተዋል፡፡ አርሶና አርብቶ አደሩም የሚቀርብለትን የአፈር ማዳበሪያ በአግባቡ በመጠቀም የግብርና ልማት ስራዎችን እንዲያከናውኑ መልዕክት አስተላልፈዋል፡፡ የአፈር ማዳበሪያ የማጓጓዙን ስራ ለማከናወን ከ10 ሺህ በላይ የየብስ ተሸከርካሪዎችን በማሰማራት እየተሰራ ሲሆን ከዚህ በተጨማሪም ከ16 በላይ የባቡር ማጓጓዣዎችንም በመጠቀም ወደብ የደረሰውን የአፈር ማዳበሪያ ወደ አገር ውስጥ የማስገባት ስራ እየተሰራ መሆኑን ዶ/ር ዓለሙ ጠቁመዋል፡፡ ከዚህ ጋር በተያያዘም የ2016/17 በጀት ዓመት የአፈር ማደበሪያ አገባብ ዕቅድ እና ክንውን ላይ የስትሪንግ ኮሚቴ ውይይት ተካሂዷል፡፡
ካሜራ፡- ያሬድ አሰፋ
ዘጋቢ፥- ሰለሞን ደምሰው

ኮርፖሬሽኑ 10 አጭዶመውቂያዎችንተረከበ

አዲስ አበባ፣ ህዳር 11/ 2016 ዓ.ም. (ኢግሥኮ)፡- የኢትዮጵያ የግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን ከቻይና ያስመጣቸውን ‘ዙምላየን’ በመባል የሚታወቁ 10 አጭዶ መውቂያዎችን (combine harvesters) ዛሬ ህዳር 11 ቀን 2016 ተረከበ፡፡ የአጭዶ መውቂያዎቹን ቁልፍ የዙምላየን ካምፓኒ ተወካይ ሚስተር አሊን ኪን ለኮርፖሬሽኑ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ክፍሌ ወልደማርያም አስረክበዋል፡፡

በርክክቡ ወቅት አቶ ክፍሌ እንደተናገሩት፣ የቻይና የእርሻ እና የኮንስትራክሽን መሣሪያዎች አምራች ኩባንያ ከሆነው ዙምላየን ጋር ኮርፖሬሽኑ የንግድ ስምምነት በመፈጸም ለመጀመሪያ ጊዜ አጭዶ መውቂያ መሣሪያዎችን ለአርሶ አደሮች፣ በግብርና ሥራ ለተሰማሩ ድርጅቶች እና ባለሀብቶች ማቅረቡን ገልጸዋል። አጭዶ መውቂያዎቹ ብልሽት ሲያጋጥማቸው በቀላሉ የሚጠገኑ፣ ለአያያዝና አጠቃቀም ምቹ እና ለሀገራችን የአየር ንበረትና የመሬት አቀማመጥ ተስማሚ በመሆናቸው በአብዛኛው ተጠቃሚዎች ዘንድ ተመራጭነት እንደሚኖራቸው አቶ ክፍሌ አስታውቀዋል፡፡

የዙምላየን ተወካይ አሊን ኪን በበኩላቸው፣ አጭዶ መውቂያዎቹን ለማስተዋወቅ በመገኘታቸው ክብር እንደሚሰማቸው ጠቁመው፣ ዙምላየን ኩባንያ በቻይና ግንባር ቀደም የኮንስትራክሽን እና እርሻ መሣሪያዎች አምራች መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ኩባንያቸው የእርሻ መሣሪያዎችን በማቅረብ ረገድ የስኬት ታሪክ ያለው መሆኑን አንስተው፣ ከኮርፖሬሽኑ ጋር ከሽያጭ በኋላ በተለያዩ የቴክኒክ እና ሞያ ድጋፎች አብረው እንደሚሰሩና በዚህም ስኬታማ እንደሚሆኑ አስረድተዋል፡፡ በሌላ በኩል አጭዶ መውቂያዎቹ በምርት መሰብሰብ ወቅት የሚከሰት ብክነትን በማስቀረት ምርታማነትን እንደሚጨምሩም ተናግረዋል፡፡ ከርክክቡ ቀጥሎ የአጭዶ መውቂያዎቹ የትውውቅ ፕሮግራም የተካሄደ ሲሆን፤ አጭዶ መውቂያው ስንዴ፣ በቆሎ፣ ጤፍ፣ አኩሪ አተር እና ሌሎች የሰብል አይነቶችን ማጨድና መውቃት እንደሚችል በባለሞያዎች ተብራርቷል። በአንድ ጊዜ እስከ አራት ሜትር ስፋት ያለው ሰብል አጭዶ መውቃት እንደሚችል የተነገረለት ዙምላየን አጭዶ መውቂያ፣ 25 ኩንታል የመያዝ አቅም ያለው ጎተራ/ቋት እንዳለው በትውውቁ ላይ ተገልጿል። በዋናው መሪያ ቤት ግቢ በተካሄደው የርክክብ ሥነ ሥርዓት ላይ ከዙምላየን የመጡ የቴክኒክ ባለሞያዎች፣ የኮርፖሬሽኑ የሥራ አመራር ቦርድ አባል፣ የሥራ መሪዎች፣ የመሠረታዊ የሠራተኛ ማኅበር ሰብሳቢ እና ሠራተኞች ተገኝተዋል፡፡ ከዙምላየን የመጡ የቴክኒክ ባለሞያዎች ከህዳር 7-8/2016 ዓ.ም ስለ አጭዶ መውቂያው ለኮርፖሬሽኑ ኦፕሬተሮችና መካኒኮች የቴክኒክ ሞያ ሥልጠና ሰጥተዋል፡፡ የኢትዮጵያ የግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን የግብርና ግብዓቶችን እና የእርሻ መሣሪያዎችን በተመጣጣኝ ዋጋ ለተጠቃሚዎች በማቅረብ፣ ከማሳ ዝግጅት እስከ ጎተራ የሚዘልቅ የተቀናጀ የሜካናይዜሽን አገልግሎት በመስጠት እንዲሁም አዳዲስ የግብርና ቴክኖሎጂዎችን በማስተዋወቅ የሀገሪቷን ግብርና ለማዘመን እየሰራ ይገኛል። ኮርፖሬሽኑ በአሁኑ ወቅት የቼክ ሪፐብሊክ ስሪት የሆነውን ‘ዜቶር’ ትራክተር እና ሌሎች የእርሻ መሣሪያዎችን ከአውሮፓ እና ቻይና በማስመጣት ለተጠቃሚዎች በማቅረብ ላይ ይገኛል፡፡

የኮርፖሬሽኑ ዋና ሥራ አስፈጻሚ የምርት መሰብሰብ ሥራ አስጀመሩ ለበጋ መስኖ ስንዴ ልማት የሚውል ዘር እየተሰበሰበ ነው

አርዳይታ፣ ህዳር3/2016 ዓ.ም (ኢግሥኮ):- በኢትዮጵያ የግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን የአርዳይታ ቅድመ መስራች፣ መስራች እና የተመሰከረለት ዘር እርሻ ልማት የደረሰ ምርት የመሰብሰብ ሥራን የኮርፖሬሽኑ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አስጀመሩ። ዋና ሥራ አስፈጻሚው አቶ ክፍሌ ወልደማርያም ዛሬ ህዳር 3 ቀን 2016 ዓ.ም በአርዳይታ የዘር ማባዣ እርሻ ልማት ተገኝተው የምርት መሰብሰብ ሥራን አስጀምረዋል። የእርሻ ጣቢያው በ2015/16 የምርት ዘመን የስንዴ፣ ገብስ፣ ጎመን ዘር እና በቆሎ ሰብሎች 20 ዝርያዎችን ማባዛቱን የገለጹት አቶ ክፍሌ፣ በቅድመ መስራች፣ መስራች እና የተመሰከረለት ዘር ከተሸፈነው 3 ሺህ 69.32 ሄክታር መሬት ከ82 ሺህ ኩንታል በላይ ዘር እንደሚጠበቅ አስታውቀዋል። ከሚሰበሰበው ዘር ውስጥ ለበጋ መስኖ ልማት የሚውል የስንዴ ዘር ዋነኛው መሆኑንም አክለው ተናግረዋል። በሀገር ደረጃ በምርጥ ዘር አቅርቦት ፋና ወጊ የሆነው የኢትዮጵያ የግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን በተለያዩ ክልሎች አምስት አካባቢዎች የቅድመ መስራች፣ መስራች እና የተመሰከረለት ዘር ማባዣ እርሻ ልማት ጣቢያዎችን (አርዳይታ፣ ጎንዴ ኢተያ፣ ጊቤ፣ ቻግኒ እና ታማሻሎ) በማቋቋም እንዲሁም በሰፋፊ የመንግሥትና የግል እርሻዎች እና በክላስተር በተደራጁ አርሶ አደሮች ማሳዎች በኮንትራት በመስራት በአማካይ በ15 ሺህ ሄክታር መሬት የ22 ሰብሎችን 78 ዝርያዎች እያባዛ በዓመት ከ350 ሺህ ኩንታል በላይ ዘር ለተጠቃሚዎች እያቀረበ ይገኛል፡፡ ይህም ኮርፖሬሽኑ በሀገር ደረጃ ካለው የምርጥ ዘር ፍላጎት ውስጥ ከ30 በመቶ በላይ የሚሆነውን ድርሻ እንዲያሟላ አስችሎታል፡፡ ኮርፖሬሽኑ በ2015/16 ምርት ዘመን በሦስት የዘር ደረጃዎች በእራሱ የምርጥ ዘር ማባዣ እርሻዎች፣ በሰፋፊ ኮንትራት አባዥዎች እና በክላስተር በተደራጁ አርሶ አደሮች ማሳዎች በዘር ከሸፈነው 20 ሺህ ሄክታር የሚጠጋ መሬት 473 ሺህ 791 ኩንታል ዘር ይገኛል ተብሎ ይጠበቃል። የሀገሪቷን ግብርና ለማዘመን በአንድ መስኮት የተሟላ አገልግሎት በመስጠት ላይ የሚገኘው ኮርፖሬሽኑ፣ የተለያዩ የግብርና ግብዓቶችንና የእርሻ መሣሪያዎችን ለተጠቃሚዎች ከማቅረቡ ባሻገር የተቀናጀ የግብርና ሜካናይዜሽን፣ የደረቅ ጭነት እንዲሁም ከሽያጭ በኋላ የቴክኒክና ሞያ፣ የምክርና የጥገና አገልግሎቶችን ተደራሽ በማድረግ ላይ ይገኛል።