* በ2018 በጀት ዓመት ካለፉት ዓመታት የላቀ ውጤት ማምጣት እንደሚጠበቅበትም ተገልጿል
አዲስ አበባ፣ ነሐሴ 22 ቀን 2017 ዓ.ም (ኢግሥኮ)፦ የኢትዮጵያ የግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን የ2017 በጀት ዓመት ዕቅድ አፈጻጸም ከፍተኛ መሆኑን የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግስ (ኢኢሆ) አስታወቀ።
የኮርፖሬሽኑ የ2017 በጀት ዓመት አፈጻጸምና የ2018 በጀት ዓመት ዕቅድ ነሐሴ 22 ቀን 2017 ዓ.ም በግዮን ሆቴል በተገመገመበት ወቅት ኮርፖሬሽኑ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ያስመዘገበው አፈጻጸም ከፍተኛ መሆኑ ተገልጿል። የውይይት መድረኩን የመሩት የኢኢሆ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ብሩክ ታዬ (ዶ/ር) ፣ ተቋሙ በ2018 በጀት ዓመት ካለፉት ዓመታት የላቀ ውጤት ማምጣት ይጠበቅበታል ብለዋል። ከዚህ አኳያም ኮርፖሬሽኑ አዳዲስ ተጨማሪ የእርሻ መሬቶችን በስፋት በማልማት ወደ ሌላ ዓመት የሚሸጋገር ትርፍ ምርት እንዲያመርት የሥራ መመሪያ ሰጥተዋል። አክለውም ከምግብ እህል ዋጋ መናር ጋር የተያያዙ እና ሌሎች በግብርናው ዘርፍ የሚታዩ ችግሮችን ለመፍታት ኮርፖሬሽኑ ከወዲሁ ዝግጁ መሆን እንዳለበት አሳስበዋል። በዚህ ረገድ ተቋሙ ለሚፈልገው ድጋፍ የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግስ ከጎኑ መሆኑን አስታውቀዋል።
ለውጭ ገበያ የሚቀርቡ የሰብል ምርቶች ላይም በስፋት መሥራት እንደሚገባ ጠቁመዋል። በግምገማው ወቅት ኮርፖሬሽኑ በምርጥ ዘርና በአፈር ማዳበሪያ አቅርቦት በየዓመቱ እድገት እያሳየ የመጣ ተቋም መሆኑ የተገለጸ ሲሆን፣ ነገር ግን ከሀገራዊ የምርጥ ዘርና የምግብ እህል ፍላጎት አንጻር ብዙ ማምረትና በክምችት መያዝ እንደሚጠበቅበት አስተያየት ተሰጥቷል።
በሌላ በኩል ተቋሙ በእንስሳት እርባታ እንዲሁም በአትክልትና ፍራፍሬ ልማት የጀመራቸውን ሥራዎች አጠናክሮ እንዲቀጥል ሀሳብ ተሰንዝሯል።
ግብርናን ማዘመን ግባችን ነው!













