የኢትዮጵያ የግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን (ኢግሥኮ) በዚህ ዓመት ከአውሮፓ ከሚያስመጣቸው 115 ትራክተሮች ውስጥ የመጀመሪያዎቹን 30 ትራክተሮች ከአንድ ወር በኋላ ይረከባል፡፡

በኮርፖሬሽኑ የእርሻ መሣሪያዎችና ሜካናይዜሽን አገልግሎት ዘርፍ ሥራ አስፈጻሚ አቶ መንግሥቱ ክፍሌ እንደተናገሩት፣ ኮርፖሬሽኑ 11.7 ሚሊዮን የአሜሪካን ዶላር ግምት ያላቸውን የተለያዩ የእርሻ መሣሪያዎች፣ ተቀጽላዎች/Implements እና መለዋወጫዎች ወደ ሀገር ውስጥ ለማስገባት ጥረት እያደረገ መሆኑን ገልጸዋል፡፡

ኤልሲ ከተከፈተላቸው የእርሻ መሣሪያዎች ውስጥ የቼክ ሪፐብሊክ ስሪት የሆኑት 115 ትራክተሮች እንደሚገኙበት የገለጹት አቶ መንግሥቱ፣ ከእነዚህ ውስጥ 30ዎቹ ትራክተሮች ከመጪው ጥር ወር አጋማሽ ጀምሮ አዲስ አበባ ይደርሳሉ ብለዋል፡፡

ዘመናዊ የእርሻ መሣሪያዎች የሀገራችንን የግብርና አመራረት ዘዴ ለማዘመን ከፍተኛ ፋይዳ አላቸው ያሉት አቶ መንግሥቱ፣ ከዚህ አኳያ ትራክተሮቹ ለክልሎች፣ ለአርሶ አደሮች፣ በግብርና ሥራ ለተሰማሩ የግል ባለሃብቶች እና ለሌሎች ተጠቃሚዎች እንደሚቀርቡም አክለው አስታውቀዋል፡፡

ኮርፖሬሽኑ የሚያስመጣቸው ‘ዜቶር’ በመባል የሚታወቁት ትራክተሮች ለአጠቃቀም ቀላል መሆናቸውን እንዲሁም የአጠቃቀምና አያያዝ ጉድለት ቢያጋጥም እንኳ በቶሎ እንደማይበላሹ የገለጸት ሥራ አስፈጻሚው፣ ብልሽት ካጋጠማቸውም በቀላሉ ሊጠገኑ እንደሚችሉ አብራርተዋል፡፡

በመጨረሻም ኮርፖሬሽኑ ከእርሻ መሣሪያዎች ሽያጭ በኋላ የጥገና፣ የቴክኒክ ሞያ ሥልጠና እና የመለዋወጫዎች አቅርቦት አገልግሎት እንደሚሰጥ ተናግረዋል፡፡