አዲስ አበባ፣ ጥቅምት 11/2015 ዓ.ም (ኢግሥኮ) በኢትዮጵያ የግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን በአሰላ ቅርንጫፍ ጽ/ቤት አማካኝነት በጎንዴ ኢተያ መስራች ዘር ማባዣ እርሻ ልማት እንዲሁም በሰፋፊ የባለሃብትና የአርሶ አደር የኮንትራት እርሻዎች በዘር ከተሸፈነው 3 ሺህ 15 ሄክታር መሬት ከ111 ሺህ ኩንታል በላይ ምርት እንደሚጠበቅ ተገለጸ፡፡

የቅርንጫፍ ጽ/ቤቱ ሥራ አስኪያጅ አቶ ብርሃኑ የሺጥላ እንደገለጹት፣ ቅርንጫፍ ጽ/ቤቱ የራሱ እርሻዎች በሆኑት የጎንዴ ኢተያ እንዲሁም በሰፋፊ የባለሃብት እርሻዎች እና በአርሶ አደር ማሳ የ11 ሰብል ዓይነቶች 38 ዝርያዎች እየተባዙ ይገኛሉ፡፡

በ2014/15 የመኸር ወቅት 1 ሺህ 561 ሄክታር መሬት በዘር ለመሸፈን ታቅዶ 3 ሺህ 15 ሄክታር በዘር ለመሸፈን ተችሏል ያሉት አቶ ብርሃኑ፣ በዚህም ከ111 ሺህ ኩንታል በላይ ምርት ይገኛል ተብሎ እንደሚጠበቅ አስታውቀዋል፡፡

የዘር ብዜት ሥራው በኦሮሚያ ክልል ምስራቅ ሸዋ እና አርሲ ዞኖች እየተካሄደ እንደሚገኝ የገለጹት ሥራ አስኪያጁ፣ በዋናነት በቢሾፍቱ፣ ወንጂ፣ ባቱ፣ በቆጂ እና ዴራ አካባቢዎች ባሉ ሰፋፊ እርሻዎችና ማሳዎች እንደሆነ ጠቁመዋል፡፡

በአሁኑ ወቅት በአበባ ደረጃ ያለ፣ ፍሬ መያዝ የጀመረ እና የደረሰ ሰብል አለ ያሉት አቶ ብርሃኑ፣ በወንጂ ሸዋ ስኳር ፋብሪካ የተዘራው የስንዴ ሰብል በመድረሱ እየተሰበሰበ ይገኛል ብለዋል፡፡

በሌላ በኩል በአሰላ ከተማ በሚገኘው የቅርንጫፍ ጽ/ቤቱ ዘር ማዘጋጃ ማሽን ለግብርና ምርምር ተቋማት፣ ለዘር አባዥዎች እና ለሌሎች ተጠቃሚዎች የዘር ብጠራ አገልግሎት እየሰጡ መሆኑን አብራርተዋል፡፡

አክለውም የአፈር ማዳበሪያ፣ የአግሮኬሚካሎች እና የዘር ሽያጭ እያከናወኑ እንደሚገኙ ገልጸዋል፡፡

በኢትዮጵያ የግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን (ኢግሥኮ) ስር የሚተዳደረው የአሰላ ቅርንጫፍ ጽ/ቤት በ1973 ዓ.ም የተቋቋመ ሲሆን፤ በራሱ የመስራች ዘር ማባዣ እርሻ ጣቢያ እና በኮንትራት እርሻዎች እያባዛ ከሚገኘው ዘር በተጨማሪ ለአርሶ አደሩ፣ ለባለሃብቶች እና ለልማት ድርጅቶች የግብርና ማሳደጊያ ግብዓቶችን እያቀረበ ይገኛል፡፡

### ግብርናን ማዘመን ግባችን ነው!