የኢትዮጵያ የግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን Ethiopian Agricultural Businesses Corporation

የግብርና ሚኒስትሩና የኮርፖሬሽኑ የሥራ አመራር ቦርድ የአሰላ ቅርንጫፍ ጎንዴ ኢተያ እርሻ ጣቢያዎችን ጎበኙ

የግብርና ሚኒስትሩና የኢትዮጵያ የግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን የሥራ አመራር ቦርድ የአሰላ ቅርንጫፍ ጎንዴ ኢተያ እርሻ ጣቢያዎችን ነሐሴ 16/2013 ዓ.ም ጎበኙ።

በጉብኝቱ ወቅት የተገኙት የኢፌዲሪ የግብርና ሚኒስቴር ሚኒስትር አቶ ዑመር ሁሴን፣ የኢትዮጵያ የግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን የሥራ አመራር ቦርድ ሰብሳቢ ዶክተር ግርማ አመንቴ እና የኮርፖሬሽኑ የቦርድ አባላት አሰላ ቅርንጫፍ ጎንዴ ኢተያ እርሻ ጣቢያዎች ላይ የተዘሩ የጤፍ፣ ስንዴ፣ ባቄላ፣ ጎመን፣ ተልባ፣ ሽምብራና በቆሎ የሰብል ዘሮችን ተዘዋውረው ተመልክተዋል።

 በተጨማሪም የአሰላ ቅርንጫፍ የምርጥ ዘር መጋዘንና የዘር ማበጠሪያ (ማዘጋጃ) ማሽን ጎብኝተዋል።

 ከጉብኝቱ በኋላ በተደረገ ውይይት አስተያየታቸውን የሰጡት የኮርፖሬሽኑ የሥራ አመራር ቦርድ ሰብሳቢ ዶክተር ግርማ አመንቴ በተመለከቱት የልማት ሥራ መደሰታቸውን ገልጸዋል።

አክለውም ኮርፖሬሽኑ ለምርጥ ዘር ማባዣ የሚውል ተጨማሪ መሬት ለማግኘት የሚያደርገውን ጥረት አጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት ጠቁመው፣ በተለይም የአርሶ አደሩን ማሳ ለዘር ማባዣነት ለመጠቀም የጋራ ተጠቃሚነትን መሰረት ያደረገ የኮንትራት እርሻ የአሠራር ስምምነት (contractual farming system) መተግበር እንዳለበት አስታውቀዋል።

 በዚህ የአሠራር ስምምነት አርሶ አደሩ የእርሻ መሬቱን ተጠቅሞ ኮርፖሬሽኑ የሚያቀርብለትን ምርጥ ዘር ካባዛ በኋላ ኮርፖሬሽኑ ምርቱን መልሶ ስለሚገዛው የበርካታ ሰብል ዝርያዎችን ዘር በአርሶ አደሩ ማሳ ላይ ማባዛት እንደሚቻል አስረድተዋል።

በአስተያየታቸው ማጠቃለያም የግብርናውን ዘርፍ ለማዘመን ኮርፖሬሽኑ የተሰጠውን ተልዕኮ ይበልጥ መወጣት እንዲችል ከአርሶ አደር ጋር በሚደረግ የኮንትራት እርሻ ስምምነት፣ በአፈር ማዳበሪያ ግብይትና ፋይናንስ ሥርዓት ፖሊሲ፣ በሚወገድ ማዳበሪያ፣ በፋይናንስ እና አፋጣኝ መፍትሔ በሚያስፈልጋቸው ሌሎች ጉዳዮች ዙሪያ የግብርና ሚኒስቴር እገዛ እንደሚያስፈልግ ተናግረዋል።

 የግብርና ሚኒስትሩ አቶ ዑመር ሁሴን በበኩላቸው በተመለከቱት ሁሉ መደሰታቸውን ገልጸው፣ ኮርፖሬሽኑ የዘር ብዜት ሥራውን ይበልጥ ማስፋትና ማሳደግ እንደሚጠበቅበት ተናግረዋል።

አያይዘውም ኮርፖሬሽኑ ያጋጠሙትን ተግዳሮቶች ለመፍታት የተቋሙ የሥራ አመራር ቦርድ ጉዳዩ የሚመለከታቸው የባለድርሻ አካላት የሚሳተፉበት የውይይት መድረክ እንዲያዘጋጅ ጠይቀዋል።

 ይህን በተመለከተም የኮርፖሬሽኑ የቦርድ ሰብሳቢ ዶክተር ግርማ አመንቴ በቅርቡ አንድ የምክክር መድረክ እንዲዘጋጅ ለኮርፖሬሽኑ ማኔጅመንት የሥራ መመሪያ ሰጥተዋል።  በኢትዮጵያ የግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን የአሰላ ቅርንጫፍ ጎንዴ ኢተያ እርሻ ጣቢያዎች በ2013/14 የሰብል ዘመን የመኸር ወቅት በ389 ሄክታር መሬት ላይ በ10 ሰብሎች 36 የተለያዩ ቅድመ መስራች እና መስራች ዝርያዎች ተዘርተዋል።

ኮርፖሬሽኑን ወደ ተሻለ የእድገት ምዕራፍ የሚያሸጋግሩ አዳዲስ ሃሳቦችን ማፍለቅ እንደሚገባ ተገለጸ

“ኮርፖሬሽኑ ካለው አፈጻጸምና ልምድ አንጻር በ2014 በጀት ዓመት የተሻለ ውጤት እንደሚያስመዘግብ ተስፋ አደርጋለሁ” የኮርፖሬሽኑ የሥራ አመራር ቦርድ ሰብሳቢ

የኢትዮጵያ የግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽንን ወደ ተሻለ የእድገት ምዕራፍ የሚያሸጋግሩ አዳዲስ ሃሳቦችን ማፍለቅ እንደሚገባ የኮርፖሬሽኑ የሥራ አመራር ቦርድ ሰብሳቢ ገለጹ፡፡

የቦርድ ሰብሳቢው ዶክተር ግርማ አመንቴ ይህንን የገለጹት ነሐሴ 22/2013 ዓ.ም በተካሄደ የኮርፖሬሽኑ የሠራተኞች አመታዊ ስብሰባ ላይ ነው፡፡

በስብሰባው ወቅት የተቋሙ የ2013 በጀት ዓመት አፈጻጸምና የ2014 በጀት ዓመት ዕቅድ ቀርቦ ውይይቱን የቦርድ ሰብሳቢው መርተውታል፡፡

በ2013 በጀት ዓመት የተገኘውን አበረታች ውጤት ያደነቁት ሰብሳቢው፣ እያንዳንዱ ሠራተኛ እኔ ሰርቼ ያመጣሁት ውጤት ነው የሚል አስተሳሰብ ማዳበር እንዳለበት አስረድተዋል፡፡

ይሁንና በአንዱ ትክሻ ሌላው ቁጭ ብሎ ሳይሰራ መጠቀም እንደሌለበትም አስገንዝበዋል፡፡ ከሥራ ክፍል አኳያም አንዱ ያተረፈውን ሌላው እየበላ ኮርፖሬሽኑን ለኪሳራ መዳረግ እንደሌለበት አሳስበዋል፡፡

ኮርፖሬሽኑ ባለው የእርሻ መሬት ሁለቴና ሦስቴ ማምረት እንደሚጠበቅበት የገለጹት ዶክተር ግርማ፣ ከዚህ ባሻገር ከክልሎች ጋር በቅርበት በመነጋገርና በመስራት ተጨማሪ አዳዲስ የእርሻ መሬቶችን ማፈላለግና ማልማት እንደሚያስፈልግ ጠቁመዋል፡፡

የኮርፖሬሽኑን የ2014 በጀት ዓመት ዕቅድ አስመልክተው ሲናገሩም ድርጅቱ ካለው አፈጻጸምና ልምድ አንጻር በበጀት ዓመቱ የተሻለ ውጤት እንደሚያስመዘግብ ተስፋ አደርጋለሁ ብለዋል፡፡ ለዕቅዱ ስኬትም እንደምንግዜውም ሁሉ የቦርዱ ድጋፍና ክትትል እንደማይለይ በራሳቸውና በሥራ አመራር ቦርዱ ስም አረጋግጠዋል፡፡

የእለቱን ስብሰባ በንግግር የከፈቱት የኮርፖሬሽኑ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ክፍሌ ወልደማርያም በበኩላቸው፣ ኮርፖሬሽኑ ከተቋቋመበት ከ2008 ዓ.ም ጀምሮ በማኔጅመንቱና በሠራተኛው ከፍተኛ ጥረት እንዲሁም በተቋሙ የሥራ አመራር ቦርድ እና በመንግሥት የልማት ድርጅቶች ይዞታና አስተዳደር ኤጀንሲ ሁለገብ ድጋፍ በየአመቱ ትርፋማነቱን አስጠብቆ መዝለቁን ተናግረዋል፡፡

“በተለይም በ2013 በጀት ዓመት በኮሮና ቫይረስ በሽታ ወረርሽኝ፣ በጸጥታ ችግሮችና በውጭ ምንዛሪ እጥረት ሳቢያ ባጋጠመን ፈታኝ ሁኔታ ውስጥ ሆነን የተገኘ ትርፍ አፈጻጸም ካለፉት አራት ዓመታት አማካይ እና ከ2012 በጀት አመት አፈጻጸም ጋር ሲነጻጸር በቅደም ተከተል 42% እና 8% እድገት አሳይቷል” ብለዋል፡፡

ለውጤቱ መሳካትም የበኩላቸውን ድጋፍ ላደረጉ የኮርፖሬሽኑ የሥራ አመራር ቦርድ አባላት፣ የመንግሥት የልማት ድርጅቶች ይዞታና አስተዳደር ኤጀንሲ እና በገንዘብ ሚኒስቴር የመንግሥት ልማት ድርጅቶች ክትትልና ድጋፍ ዳይሬክቶሬት ምስጋና አቅርበዋል፡፡

በተመሳሳይ የተቋሙ የመሰረታዊ የሠራተኛ ማኅበር፣ መላው የሥራ ኃላፊዎችና ሠራተኞች ለኮርፖሬሽኑ ዕቅድ መሳካት ላበረከቱት አስተዋጽዖ በኮርፖሬሽኑ እና በራሳቸው ስም አመስግነዋል፡፡ በስብሰባው ላይ የሥራ አመራር ቦርድ አባላት፣ የመንግሥት የልማት ድርጅቶች ይዞታና አስተዳደር ኤጀንሲ እና የገንዘብ ሚኒስቴር የሥራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል፡፡