አዲስ አበባ፣ ሐምሌ 14 ቀን 2018 ዓ.ም (ኢግሥኮ)፡- የኢትዮጵያ የግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን የበላይ አመራሮች በአፈር ማዳበሪያ አቅርቦት ዙሪያ የሳውዲ አረቢያ የመንግሥት የልማት ድርጅት ከሆነው የማዕድን ኩባንያ (ማአደን/MA’ADEN) ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች ጋር በዋናው መሥሪያ ቤት ተወያዩ።
የኮርፖሬሽኑ የግብርና ግብዓት አቅርቦት ዘርፍ ሥራ አስፈጻሚ አቶ በእውቀቱ ያረጋል እንደገለጹት፣ ውይይቱ በዋናነት ያተኮረው ኩባንያው ከኢትዮጵያ መንግሥት ጋር ቀጥተኛ የግዥ ስምምነት (መንግሥት ለመንግሥት/G2G/ ስምምነት) በመፈጸም ለሚቀጥሉት ሦስት ዓመታት የ«ዳፕ» (DAP) አፈር ማዳበሪያን በተሻለ ዋጋና ጥራት ማቅረብ በሚችልበት ሁኔታ ላይ ነው።
በተጨማሪም ኩባንያው ለኢትዮጵያ አርሶ አደሮች በአፈር ማዳበሪያ አጠቃቀምና አተገባበር ዙሪያ የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥልጠናዎችን መስጠት በሚችልበት የትብብር መስክ ላይ ምክክር ተደርጓል።
ከኩባንያው ማዳበሪያን በቀጥታ መግዛት በርካታ ዘላቂ ጥቅሞች ያሉት ሲሆን፣ በተለይም ሳውዲ አረቢያ ለኢትዮጵያ ካላት የጂኦግራፊ ቅርበት አኳያ የዳፕ ማዳበሪያን በአጭር ቀናት ውስጥ አጓጉዞ ለአርሶ አደሩ በወቅቱ ለማሰራጨት ያስችላል፡፡
ከዚህ ባሻገር የመጓጓዣ ወጪን ለመቀነስና የጥራት ደረጃን ለመጠበቅ ከፍተኛ ፋይዳ ይኖረዋል።
የሳውዲው ኩባንያ – «ማአደን» በአሁኑ ወቅት ለኮርፖሬሽኑ ማዳበሪያ በማቅረብ ላይ ሲሆን፣ በአሜሪካ፣ እስራኤልና ኢራን ግጭት ምክንያት የሆርሙዝ ሰርጥ በተዘጋበት ወቅት ግብዓቱን በየብስና በቀይ ባሕር በኩል በአማራጭ መንገዶች በማጓጓዝ የአቅርቦት እጥረት እንዳይፈጠር ላደረገው ጥረት ኮርፖሬሽኑ ምስጋና አቅርቦለታል።
በቀጣይ ኩባንያው ከኮርፖሬሽኑ የሥራ አመራር ቦርድና ከግብርና ሚኒስቴር አመራሮች ጋር ከተወያየ በኋላ መደበኛ ስምምነት እንደሚፈረም ይጠበቃል።
###
ግብርናን ማዘመን ግባችን ነው!


