አዲስ አበባ፤ መጋቢት 8/2018(ኢዜአ)፦ ዲጂታል ቴክኖሎጂን በመጠቀም የአርሶ አደሩን የፋይናንስ አቅም ማሻሻልና የግብርና ግብዓቶች ተጠቃሚነትን ማሳደግ የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ ወሳኝ መሆኑን የኢትዮጵያ የግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን ዋና ሥራ አስፈፃሚ የሺእመቤት ነጋሽ ገለጹ፡፡
የኢትዮጵያ የግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን እና የግሪን አግሮ ሶሉሽን ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ኩባንያ “ለእርሻ” በጋራ ለመሥራት የሚያስችላቸውን የመግባቢያ ስምምነት ተፈራረመዋል።
ስምምነቱን የኢትዮጵያ የግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን ዋና ሥራ አስፈፃሚ የሺእመቤት ነጋሽ እና የግሪን አግሮ ሶሉሽን ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ኩባንያ “ለእርሻ” ሥራ አስፈፃሚ አብረሃም እንዲሪያስ ተፈራርመዋል።
ስምምነቱ የዲጂታል ቴክኖሎጂን በመጠቀም አርሶ አደሮችን የፋይናንስ አቅም ለማሻሻልና የግብርና ግብዓቶች ተጠቃሚነትን ለማሳደግ ያለመ እንደሆነ ተመልክቷል።
የኢትዮጵያ የግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን ዋና ሥራ አስፈፃሚ የሺእመቤት ነጋሽ በዚሁ ጊዜ እንደተናገሩት ኮርፖሬሽኑ የግብርናውን ዘርፍ ለማዘመንና ምርታማነትን ለመጨመር እየሰራ ይገኛል።
ስምምነቱ አርሶ አደሩ የግብርና ግብዓቶችን፣ የፋይናንስ አገልግሎቶችንና የሜካናይዜሽን አማራጮችን በቀላሉ ማግኘት የሚችልበትን መንገድ ለመፍጠር ያለመ ነው ብለዋል።
በዚህም መሰረት ብሔራዊ የግብርና ፍኖተ ካርታ እና ፋይናንስ አካታችነት ትግበራ ላይ በጋራ በመስራት እስከ 2030 ድረስ ለአንድ ሚሊየን አነስተኛ አርሶ አደሮች የብድር እድል ለማመቻቸት የተያዘውን እቅድ ለማሳካት እንደሆነ ተናግረዋል፡፡


