በአዲስ አበባ፣ የካቲት 13 ቀን 2018 ዓ.ም (ኢግሥኮ):- የኢትዮጵያ የግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን የተለያየ የፈረስ ጉልበት ያላቸውን 18 ትራክተሮችን ለፊንጫ ስኳር ፋብሪካ የካቲት 13 ቀን 2018 ዓ.ም በሽያጭ አስረከበ፡፡
ትራክተሮቹ ዜቶር እና ዲዩዝ ፋር ተብለው የሚታወቁ የአውሮፓ ስሪት ሲሆኑ፣ ከ106 እስከ 166 የፈረስ ጉልበት አላቸው።
በኮርፖሬሽኑ ዋና መስሪያ ቤት በተካሄደው የርክክብ ሥነ ሥርዓት ላይ የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግስ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ብሩክ ታዬ (ዶ/ር)፣ የኮርፖሬሽኑ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ወ/ሮ የሺእመቤት ነጋሽ፣ የፊንጫ ስኳር ፋብሪካ ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ መንግሥቱ ኃይለማርያም እና ሌሎች የሆልዲንጉና የኮርፖሬሽኑ የሥራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል፡፡
ኮርፖሬሽኑ ለደንበኞች ለሚያቀርባቸው የእርሻ መሣሪያዎች በሚሰጠው የድህረ ሽያጭ አገልግሎት መሰረት ለፊንጫ ስኳር ፋብሪካ ትራክተር ኦፕሬተሮችና መካኒኮች የሁለት ቀናት የቴክኒክ ሥልጠና መስጠቱን የኮርፖሬሽኑ የእርሻ መሣሪያዎችና መለዋወጫዎች ማርኬቲንግ መረጃና ቴክኒካል ድጋፍ ሰጪ ቡድን መሪ ወ/ሮ ናፈቁሽ ደሴ ገልጸዋል፡፡
የኢትዮጵያ የግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን ዘመናዊ እርሻዎችን ለማስፋፋትና ግብርናን ለማዘመን የሚያስችሉ የእርሻ መሣሪያዎችን ከነመለዋወጫቸው በተመጣጣኝ ዋጋ ለተጠቃሚዎች እያቀረበ ይገኛል፡፡
###
ግብርናን ማዘመን ግባችን ነው!



