አዲስ አበባ፣ የካቲት 13 ቀን 2018 ዓ.ም (ኢግሥኮ):- የኢትዮጵያ የግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን ትላልቅ የሜካናይዝድ እርሻዎችን በማስፋፋት የግብርና ምርታማነትን ማሳደግና የሀገሪቷን የምግብ ሉዓላዊነት ማረጋገጥ ላይ ቅድሚያ ሰጥቶ እንዲሠራ የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግስ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ብሩክ ታዬ (ዶ/ር) አሳሰቡ፡፡
ዋና ሥራ አስፈጻሚው ይህንን ማሳሰቢያ የሰጡት፣ ሆልዲንጉ የተቋሙን የ2018 በጀት ዓመት የመጀመሪያ መንፈቅ የሥራ አፈጻጸም በኮርፖሬሽኑ ዋና መስሪያ ቤት የካቲት 13 ቀን 2018 ዓ.ም በገመገመበት ወቅት ነው፡፡
ዋና ሥራ አስፈጻሚው ኮርፖሬሽኑ በግብርናው ዘርፍ ትልቅ አቅምና የካበተ ልምድ ያለው ተቋም መሆኑን ጠቅሰው፣ በሀገሪቷ ያልታረሰ መሬትን በማልማት ለግብርና ምርት እድገት ከፍተኛውን ድርሻ እንዲወጣ የሥራ መመሪያ ሰጥተዋል፡፡
ይህንን ለማሳካት አዲስ ስትራቴጂ በማዘጋጀት መተግበር እንደሚገባ አስታውቀው፣ የስትራቴጂው ዋና ትኩረትም ግብርናን ማስፋፋት ላይ መሆን እንዳለበት ተናግረዋል፡፡ በዚህ ረገድ ሆልዲንጉ አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግ አስታውቀዋል፡፡
በዕለቱ የኮርፖሬሽኑ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ወ/ሮ የሺእመቤት ነጋሽ፣ የኮርፖሬሽኑን የስድስት ወራት ዕቅድ አፈጻጸም ከኦፕሬሽን፣ ከገቢና ትርፍ፣ ከኮርፖሬት አስተዳደር፣ ከማኅበራዊ ኃላፊነት እንዲሁም ከሪፎርም ሥራዎች አኳያ አቅርበው የተገመገመ ሲሆን፣ ሆልዲንጉ በበኩሉ የአፈጻጸም ግብረ መልስ አቅርቧል፡፡
በኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግስ ግምገማ የተሰጡ ግብረ መልሶችን በግብዓትነት በመውሰድ በቀሪ ስድስት ወራት የኮርፖሬሽኑን አፈጻጸም ለማሻሻል ርብርብ እንደሚደረግ የኮርፖሬሽኑ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አስታውቀዋል፡፡
###
ግብርናን ማዘመን ግባችን ነው!










