የካቲት 7/2018 ዓ/ም (አሶሳ) የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ አሻደሊ ሀሰን በኢትዮጵያ ግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን ዋና ስራ አስፈፃሚ ወ/ሮ የሺመቤት ነጋሽ የተመራ ከፍተኛ የተቋሙ አመራሮች ልኡክ ጋር ተወያይተዋል።
በውይይቱ የኢትዮጵያ ግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን
የግብርናውን ዘርፍ ለማዘመንና ምርትና ምርታማነትን ለመጨመር እየተሰሩ ያሉ ስራዎችን እና የቀጣይ ትኩረት አቅጣጫዎችን አቅርበዋል።
በግብርና ሜካናይዜሽን አቅርቦት፣ በግብር ምርጥ ዘር ልማት፣ በእጣን ምርት ግብይት፣ በእንስሳት ሀብት ልማትና በአግሮ ፕሮሰሲንግ ከክልሉ መንግስት እና ከተለያዩ ማህበራት ጋር ተቀናጅቶ እንደሚሰራ ተመላክቷል።
ተቋሙ በክልሉ ለሚሰራቸው ስራዎች ስኬታማነት የክልሉ መንግስት አስፈላጊውን ድጋፍና እገዛ እንደሚያርግ ርዕሰ መስተዳድር አቶ አሻደሊ ሀሰን ገልጸዋል።
አቶ አሻደሊ አክለውም ተቋሙ ከክልሉ ግብርና ቢሮ ጋር ተናቦና ተቀናጅቶ መስራት እንደሚገባው በመጠቆም በተለይ በሜካናይዜሽን ስራዎች እንቅፋት እየሆነ ያለው የማሽነሪዎች መለዋዎጫ አቅርቦት ትኩረት ሊሰጠው ይገባል ብለዋል።
የኢትዮጵያ ግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን ዋና ስራ አስፈፃሚ ወ/ሮ የሺመቤት ነጋሽ በበኩላቸው ተቋሙ እንደ ሀገር በተለያዩ ክልሎች የምርጥ ዘር ልማት፣ የማሽነሪዎች አቅርቦቶች፣ በአግሮ ፕሮሰሲንግና የገበያ ትስስሮችን በማመቻቸት ለዘርፉ እድገት እየሰራ መሆኑን በማስታወስ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ያለውን ምቹ ሁኔታ ተጠቅሞ የተሻለ ስራ ለመስራት ያላቸውን ቁርጠኝነት ገልጸዋል።





