
አዲስ አበባ፣ መስከረም 20/2018 ዓ.ም (ኢግሥኮ)፡- የኢትዮጵያ የግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን ሥራ አመራር ቦርድ ወይዘሮ የሺእመቤት ነጋሽ ከመስከረም 16 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ የኮርፖሬሽኑ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ሆነው እንዲሠሩ መድቧል፡፡
የኢትዮጵያ ኢንደስትሪ ግብዓቶች ልማት ድርጅትን (ኢኢግልድ) ከሚያዝያ 2012 ዓ.ም እስከ መስከረም 15 ቀን 2018 ዓ.ም ድረስ በዋና ሥራ አስፈጻሚነት ከአምስት ዓመታት በላይ ያስተዳደሩት ወይዘሮ የሺእመቤት ነጋሽ፣ ከመስከረም 16 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ የኢትዮጵያ የግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን ዋና ሥራ አስፈጻሚ ሆነው ተመድበዋል፡፡
በአሁኑ ወቅት የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምክር ቤት አባል የሆኑት ወይዘሮ የሺእመቤት፣ ከመስከረም 2003 ዓ.ም ጀምሮ እስከ ሐምሌ 2013 ዓ.ም ድረስ ለሁለት ጊዜያት የኢፌዴሪ የሕዝብ ተወካዮች ም/ቤት አባልና የቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ነበሩ፡፡
በ11 ዓመታት የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ቆይታቸው የንግድና ኢንደስትሪ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ፤ የሕግ፣ ፍትሕና ዴሞክራሲ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ የንዑስና ዋና ኮሚቴ ሰብሳቢ፤ የመንግሥት ወጪ አስተዳደርና ቁጥጥር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ንዑስ ኮሚቴ ሰብሳቢ እና የከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አባል በመሆን አገልግለዋል፡፡ በተለያዩ የሥራ ኃላፊነት ቦታዎች ሀገራቸውን ያገለገሉት ወይዘሮ የሺእመቤት ነጋሽ፣ በትምህርት ዝግጅታቸው ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በሕዝብ አስተዳደርና ፖሊሲ ሁለተኛ ዲግሪ እንዲሁም ከአዳማ ዩኒቨርሲቲ በአካውንቲንግ የመጀመሪያ ዲግሪ አላቸው፡፡