“የኮርፖሬሽኑ አምባሳደር በመሆን አስፈላጊውን ድጋፍ እናደርጋለን” ብሩክ ታዬ (ዶ/ር) የኢኢሆ ዋና ሥራ አስፈጻሚ
=============================
ሀዋሳ፣ ጥቅምት 9 ቀን 2017 ዓ.ም (ኢግሥኮ):- በኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግስ (ኢኢሆ) ዋና ሥራ አስፈጻሚ ብሩክ ታዬ (ዶ/ር) የሚመራ የልዑካን ቡድን የኢትዮጵያ የግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን የምርጥ ዘር ማባዣ እርሻዎችን ጎበኘ።
የልዑካን ቡድኑ ኮርፖሬሽኑ የሚያስተዳድራቸውን የጎንዴ እና አርዳይታ የምርጥ ዘር ማባዣ እርሻዎች እንዲሁም የኮፈሌ ቅርንጫፍ ጽ/ቤት የዘር ዝግጅትን ጥቅምት 9 ቀን 2017 ዓ.ም ጎብኝቷል።
በጉብኝቱ ወቅት የኢኢሆ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ብሩክ ታዬ (ዶ/ር) ባስተላለፉት መልእክት፣ ኮርፖሬሽኑ ግብርናን ለማዘመን እያደረገ ለሚገኘው ጥረት ተቋማቸው አምባሳደር በመሆን አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግ ተናግረዋል።
አክለውም የሀገር ውስጥና የውጭ ባለሃብቶችን በማፈላለግ ከኮርፖሬሽኑ ጋር በሽርክና እንዲሰሩ ኢኢሆ የኢንቨስትመንት እድሎችን እንደሚያመቻችገልጸዋል። ኮርፖሬሽኑ የምርጥ ዘር እርሻዎችን እያስፋፋ እና ትርፋማ እየሆነ በቀጠለ ቁጥር የሚያደርጉትን ድጋፍ አጠናክረው እንደሚቀጥሉ ያስታወቁት ዋና ሥራ አስፈጻሚው፣ በተመለከቷቸው የልማት ሥራዎች መደሰታቸውን ገልጸው፣ የኮርፖሬሽኑን ሥራ አመራር እና ሠራተኞች “በርቱ፣ በጣም እንኮራባችኋለን” ብለዋል።








