የኢትዮጵያ የግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን (ኢግሥኮ) በ2015 በጀት ዓመት ለመፈጸም ያቀዳቸው ሥራዎች እንዲሳኩ የጋራ ጥረት እንዲደረግ የኮርፖሬሽኑ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አሳሰቡ፡፡

ዋና ሥራ አስፈጻሚው አቶ ክፍሌ ወልደማርያም ይህን ማሳሰቢያ የሰጡት፣ ከጥር 1 ቀን ጀምሮ ሥራ ላይ በሚውል የተከለሰ እቅድ ዙሪያ ከኮርፖሬሽኑ የሥራ ሓላፊዎችና ሠራተኞች ጋር በግብርና ምርት ማሳደጊያዎች አቅርቦት ዘርፍ የስብሰባ አዳራሽ ዛሬ ታህሳስ 11 ቀን 2015 ዓ.ም. በተደረገ ውይይት ነው፡፡

በዚሁ ወቅት አቶ ክፍሌ፤ ኮርፖሬሽኑ ተወዳዳሪ፣ ውጤታማ እና ቀጣይነት ያለው ተቋም እንዲሆን ምንጊዜም ያልተቆጠበ ጥረት ማድረግ አለብን ብለዋል፡፡

አክለውም በ2015 በጀት ዓመት የታቀዱ ሥራዎች እንዲሳኩ የግብርና ማሳደጊያ ግብዓቶች እንዲሁም የእርሻ መሣሪያዎች እና መለዋወጫዎች ግዥ በወቅቱ በመፈጸም ለአርሶ አደሩ፣ ለባለሃብቱ እና ለልማት ድርጅቶች ማቅረብ እንደሚጠበቅ አስታውቀዋል።

የኮርፖሬሽኑን ካፒታል በማሳደግ እና የሚሰጣቸውን አገልግሎቶች ተደራሽነት በማስፋት ተቋሙን ከፍተኛ ደረጃ ላይ ለማድረስ እየተሰራ መሆኑን የጠቆሙት ዋና ሥራ አስፈጻሚው፣ ለስኬቱም የኮርፖሬሽኑ የሥራ ሓላፊዎችና ሠራተኞች ‘በይቻላል እና  በጊዜ የለኝም’ የሥራ መንፈስ መረባረብ ይጠበቅባቸዋል ነው ያሉት።

የኮርፖሬሽኑ የኦፕሬሽን ዐቢይ ዘርፍ ምክትል ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ፈለቀ ገዛኸኝ በበኩላቸው፣ ኮርፖሬሽኑ በሠራተኞቹ ብቃት እንደሚተማመን ገልጸው፣ የ2015 በጀት ዓመት ዕቅድን ከመላው ሠራተኛ ጋር በመሆን እናሳካዋለን ብለዋል፡፡

አያይዘውም “እቅዱን ለማሳካት በጋራ ራዕይ አንድ ላይ መስራት እና ውጤት ማምጣት ይጠበቅብናል” በማለት ተናግረዋል፡፡

የኮርፖሬሽኑ ሠራተኞች በበኩላቸው የተቋሙ የሥራ አመራር ራዕይ ያለው፣ ሰርቶ የሚያሰራ፣ በእውቀት እና በቅንነት ሥራዎችን በአግባቡ የሚያከናውን መሆኑን ጠቁመው፤ የ2015 በጀት ዓመት ዕቅድን ለማሳካት እና የተሻለ ውጤት ለማስመዝገብ ዝግጁ መሆናቸውን አረጋግጠዋል፡፡

ኮርፖሬሽኑ በ2015 በጀት ዓመት ከ12 ቢሊዮን ብር በላይ ዋጋ ያላቸውን የግብርና ግብዓቶች፣ የእርሻ መሣሪያዎችና መለዋወጫዎች እንዲሁም የተቀናጀ የግብርና ሜካናይዜሽን አገልግሎት እና የደረቅ ጭነት ትራንስፖርት በተመጣጣኝ ዋጋ ለተጠቃሚዎች በማቅረብ ከታክስ በፊት 995 ሚሊዮን ብር ለማትረፍ አቅዶ እየሰራ ይገኛል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ ወቅታዊ ዓለም አቀፋዊ እና ሀገራዊ ጉዳዮች በኮርፖሬሽኑ የልማት እንቅስቃሴ ላይ ስለሚያሳድሩት ተጽዕኖ በዋና ሥራ አስፈጻሚው አቶ ክፍሌ ወልደማርያም ማብራሪያ ተሰጥቷል፡፡