የኢትዮጵያ የግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን (ኢግሥኮ) ለ2015/16 የሰብል ዘመን ከሞሮኮው የአፈር ማዳበሪያ አምራች ኦ ሲ ፒ ኩባንያ ከገዛው 7 ሚሊዮን 875 ሺህ 520 ኩንታል ማዳበሪያ (NPS family) ውስጥ የመጀመሪያው 572 ሺህ 950 ኩንታል NPS የአፈር ማዳበሪያ ጂቡቲ ወደብ ደረሰ።

ዛሬ ታህሳስ 18/2015 ዓ.ም. ከቀኑ 8:00 ላይ ወደብ የደረሰው ማዳበሪያ MV Great Comfort በተባለች የመጀመሪያዋ መርከብ ነው።

ይህ በእንዲህ እንዳለ ከሰባት ቀን በኋላ (ታህሳስ 25/2015 ዓ.ም.) 600 ሺህ ኩንታል NPSB ማዳበሪያ የጫነች MV Sea Rider የተሰኘች ሁለተኛዋ መርከብ ጅቡቲ ወደብ እንደምትደርስ ይጠበቃል።

ኮርፖሬሽኑ ለያዝነው የሰብል ዘመን የገዛው 2 ሚሊዮን 188 ሺህ 940 ኩንታል NPS እና 5 ሚሊዮን 686 ሺህ 580 ኩንታል NPSB የአፈር ማዳበሪያ በቀጣዮቹ ወራት ከሞሮኮ ወደብ ወደ ጅቡቲ ይጓጓዛል። የኢትዮጵያ የግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን (ኢግሥኮ) የግብርና ሚኒስቴር በየአመቱ አጥንቶ በሚያቀርበው ሀገራዊ የአፈር ማዳበሪያ ፍላጎት መሰረት ከ2008 ዓ.ም. ጀምሮ ማዳበሪያ ከውጭ እየገዛ የሚያቀርብ መንግሥታዊ የልማት ድርጅት ነው።