አዲስ አበባ፣ ጥቅምት 8 ቀን 2015 ዓ.ም (ኢግሥኮ)፡- በኢትዮጵያ የግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን የሀዋሳ ቅርንጫፍ ጽ/ቤት በሦስት ክልሎች በኮንትራት እርሻዎች የተለያዩ ሰብሎች ምርጥ ዘር እያባዛ ይገኛል፡፡

የቅርንጫፍ ጽ/ቤቱ ሥራ አስኪያጅ አቶ አድማሱ አናጋው እንዳስታወቁት፣ ጽ/ቤቱ በተያዘው የ2014/15 የመኸር ወቅት በኮንትራት አባዥ ሰፋፊ የባለሃብት እርሻዎች፣ በመንግሥት የግብርና ተቋማት እና በአርሶ አደር ማሳዎች ላይ በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ አርሲ እና ምስራቅ ሸዋ ዞኖች፣ በደቡብ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ክልል በጉራጌ፣ ስልጤ፣ ወላይታ፣ ሃድያ እና ሃላባ ዞኖች እንዲሁም በሲዳማ ክልል በድምሩ በስምንት ዞኖች በ2 ሺህ 34 ሄክታር መሬት ላይ የተለያዩ የሰብል ዝርያዎችን ምርጥ ዘር በማባዛት ላይ ይገኛል።

በዋናነት የስንዴ፣ ጤፍ፣ በቆሎ እና ቦለቄ ሰብሎችን ምርጥ ዘር እያባዛን ነው ያሉት አቶ አድማሱ፣ በዚህም 45 ሺህ 752 ኩንታል ዘር እንደሚገኝ ይገመታል ብለዋል፡፡

ዘር በከፍተኛ ጥንቃቄ ተመርቶ ለተጠቃሚዎች እንደሚቀርብ የገለጹት አቶ አድማሱ፣ ከዚህ አኳያ ከማሳ መረጣ ጀምሮ ምርት ተሰብስቦ መጋዘን እስኪገባ ድረስ የክትትልና የጥራት ቁጥጥር ሥራዎችን በመስክ በመገኘት እያከናወኑ መሆኑን አስረድተዋል።

የተለያዩ የሰብል ዘሮችን በማባዛት በመላ ሀገሪቱ እንደሚያሰራጩ የገለጹት ሥራ አስኪያጁ፣ በዚህ ወቅት እየተባዛ የሚገኘውን ምርጥ ዘር ጽ/ቤቱ በሀዋሳ ከተማ ባሉት ሁለት የዘር ማዘጋጃ ማሽኖች በማበጠርና በማዘጋጀት ለተጠቃሚዎች ለማቅረብ ቅድመ ዝግጅት እያደረገ እንደሚገኝ አስታውቀዋል።

አክለውም ቅርንጫፍ ጽ/ቤቱ በሻሸመኔ ከተማ ባለው የሽያጭ ማዕከል አማካኝነት የአፈር ማዳበሪያ፣ አግሮኬሚካሎች እና የእንስሳት መድሃኒቶችን ለአርሶአደሩ በቅርበት እያደረሰ መሆኑን ተናግረዋል።

በሌላ በኩል አርሶ አደሩ ከግብርና ምርምር የወጡ አዳዲስ የሰብል ዝርያዎችን እንዲጠቀም ለማስቻል በተለያዩ አካባቢዎች የሰርቶ ማሳያ እና የአርሶ አደሮች በዓል በማዘጋጀት ዝርያዎቹን የማስተዋወቅ ሥራ በትኩረት እየተከናወነ መሆኑን አመልክተዋል፡፡

### ግብርናን ማዘመን ግባችን ነው!